tgoop.com/EotcLibilery/15438
Last Update:
#የጥምቀት_በዓል_አከባበር_በአዲስ_አበባ_ከእንጦጦ_ጋራ_ጥግ_እስከ_ጃንሆይ_ሜዳ_
በአዲስ በአበባ ያሉ ገዳማትና አድባራትም በቦታ ርቀት እስከ ተለያዩበት ቀን ድረስ በእንጦጦ ጋራ ጥግ በአንድ ላይ በመፈናኘት ያድሩ ነበር፤ ኋላ ከቦታ ርቀት በኋላ የተቀሩት በጃንሆይ ሜዳ ማደር ጀምረዋል፡፡ እያደረም ሌሎች ገዳማትና አድባራት ሲመሠረቱ ከጃንሆይ ሜዳ በተጨማሪ ለአጥቢያቸው በሚቀርብ ቦታ ማደር ጀመሩ፡፡
፠ በዓለ ጥምቀት በጃን ሜዳ (ጃንሆይ ሜዳ) መከበር የጀመረው ከ1887 ዓ.ም. አንስቶ መሆኑ ይነገራል፡፡ ስያሜውምና አጀማመሩም ጃንሜዳ የሚለው ጃን፥ ጃኖ ከሚለው ጋራ የተዛመደ ሲሆን ነገሥታት ለመሾም ለመሻር፣ ዳኝነት ለመስጠት፣ ሊቃውንትን ለመሾምና፣ ዐዋጅ ሲያስነግሩ በቤተ መንግሥታቸው አቅራቢያ በሚገኝ ሜዳ ላይ የጃኖ ድንኳን ተክለው ያስነግራሉ፤ ይህም ሜዳ ከጃኖ ጋራ እየተናበበ የቦታ መጠሪያ ሁኗል፡፡ ለምሳሌ፤
‹‹ጃን ተከል›› በጎንደር ነገሥታት፤
‹‹ጃን መራቂ›› በላስታ ነገሥታት፤
‹‹ጃን ተራራ›› በአማራ ሳይንት በአፄ በዕደ ማርያም
‹‹ጃን ሜዳ›› በደብረ ታቦርና በአዲስ አበባ ናቸው፡፡
፠ አዲስ አበባ መዲና በሆነችበት ሰዓት ‹‹መሐል ሰፋሪ‹‹ የሚባሉ የመኳንንት ጕባኤ በዚሁ በጃንሜዳ በስውር ዐድማ የሚያደርጉበት ሆነ አድማውን ሲያደርጉም በጃን ሜዳ ያለው የጃኖው ድነኳን ከሩቅ እንዳይታይ በማቅ ይሸፈን ነበር፡፡ እቴጌ ጣይቱ ይህን የመሰለ ሜዳ የክፉ ምክር መምከሪያ ሆኖ ከሚኖር ተባርኮ ለጥምቀት በዓል ማክበሪያ ቢሆን ብለው ለአፄ ምኒልክ ሃሳብ አቀረቡላቸው፤ አፄ ምኒሊክም ማለፊያ ብለው ሐሳባቸውን በመቀበል ጃን ሜዳ የጥምቀት በዓል ማክበሪያ እንዲሆን አዘዙ፡፡ እንዲሁም የአፄ ምንሊክ አልጋ ወራሻቸው ልጅ ኢያሱ መሆኑን በግንቦት 10 ቀን 1901ዓ.ም. ዐዋጅ ያስነገሩበት፤ ‹‹ንሥረ ተፈሪ›› የተባለው የመጀመሪያው አውሮፕላንም በ12921ዓ.ም. ወደ ኢትዮጵያ ሲገባ ያረፈውም በዚሁ ሜዳ በመሆኑ ጭምር ስያሜው ጃንሆይ ሜዳ ተባለ፡፡
፠ በ1887ዓ.ም. በዓለ ጥምቀትን ለመጀመሪያ ጊዜ በጃን ሜዳ በሕብረት ያከበሩት የመካነ ሥላሴ ቅዱስ በዓለ ወልድ ቤተክርስቲያን፣ የመናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያንና የመንበረ መንግሥት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ነበሩ፡፡
፠ እስከ ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ መን ድረስ ግን ታቦታቱ ወደ ቀበና ወንዝ (አፈ ንጉሥ ጥላሁን ሰፈር፤ ከፈረንሳይ ኤምባሲ በታች) ከከተራው አንስቶ አድረው በጥምቀት ዕለት ወደ ጃንሜዳ ይመለሱ ነበር፡፡
ሌሎችም በየሰበካቸው በሚገኝ አምች ቦታ ሲያከብሩ ቆይተው በ1939ዓ.ም. ከንሜዳ እጅግ በጣም ብዙ ያልራቁት (የካ ሚካኤልና ቅዱስ ዑራኤል) በንጉሠ ነገሥቱ ጥሪ ተደርጎ ወደ ጃናሜዳ እንዲመጡ ተደርጎ ነበር፤ ሆኖም ሕዝብ እየበዛ ስላስቸገረ በየአቅራቢያቸው እንዲያድሩ ተድርጓል፡፡
፠ ግርማዊ ቀዳማዊ አፄ ኀይለ ሥላሴ በ1936 ዓ.ም በስፍራው የውኃ ቧንቧ እንዲዘረጋ፣ ባሕረ ጥምቀት ገንዳ በግንብ እንዲሰራ፣ የኤሌክትረክ መብራት በቦታው እንዲገባ አድርገዋል፡፡ ዙሪያውን በግንብ ተሰርቶ በቧንቧ የብረት ማገር ውብ ሆኖ እንዲታጠርና በዐፀድና በአበባዎች እንዲያጌጥ አድርገዋል፡፡ ይህ ቦታ ኋላ በ1994ዓ.ም. እድሳት ተደርጎለታል፡፡
፠ እስከ ቅርብ ጊዜያትም ድረስ ወደ ባሕረ ጥምቀት የሚወርዱ ታቦታት ከነድርባቸው ነበር፤ ለምሳሌ ቀቀጨኔ ደብረ ሰላም ከቅዱስ ገብርኤል ጋራ ነበረ፤ ኋላ ግን ድርብ ታቦታት ቀርተው ዋናውን ይዘው የሚወርዱ ሆኗል፡፡ በዚህም መሠረት በአዲስ አበባ ውስጥ እስከ 2010ዓ.ም ድረስ ….. ባሕረ ጥምቀት (አብሕርተ አጥማቃት) አሉ፡፡
፠ እስከ 1958ዓ.ም. በምስካየ ኅዙናን ተምሮ ማስተማር ማኅበርና በጠቅላይ ቤተ ክህነት የታሪክ ድርሰትና ስብከት ክፍል አስተባባሪነት ከኢ.ኦ.ተ.ቤ.ክ. ሐዋርያዊ ድርጅት፣ ከሊቃውንትና ከመምህራን፣ ከሰዋስወ ብርሃንና ከቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ በተውጣጡ መምህራን በባሕረ ጥምቀቱ የስብከተ ወንጌልና፣ የመዝሙርና የድራማ መርሐ ግብር ያቀርቡ ነበር፡፡ በ1959ዓ.ም. አካባቢ ጥቂት ሰንበት ት/ቤቶች የደንብ ልብስና ነጠላ በማድረግ ታቦታቱን አጅበው አውጥውና አጅበው በመመለስ የበዓሉ ድምቀት እየሆኑ መጡ፡፡
በአሁኑ ወቅት በጃንሜዳ የሚያድሩ ታቦታት 12 ናቸው እነርሱም፤
1ኛ. መንበረ ፀባዖት ቅድስት ሥላሴ ቤ.ክ.፤
2ኛ. ታዕካ ነገሥት በዓታ ለማርያም ገዳም፤
3ኛ. መንበረ መንግሥት ግቢ ቅዱስ ገብርኤል ገዳም፤
4ኛ. መናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤ.ክ.፤
5ኛ. ቀጨኔ ደብረ ሰላም መድኀኔ ዓለምና ደ/ትጉሃን ቅዱስ ገብርኤል ቤ.ክ.፤ (የምስካየ ኅዙናን መድኀኔ ዓለም ታቦተ ወደ ጥምቀተ ባሕር ስለማይወጣ ሕዝቡና ሰ/ት/ቤቱ አብሮ ነው የሚያከብረው)
6ኛ. መንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም
7ኛ. ደብረ ነጐድጓድ ቅዱስ ዮሐንስ ቤ.ክ.፤
8ኛ. መንበረ ልዑል ቅዱስ ማርቆስ (አብሮም ቅዱስ ሚካኤል ይወርዳል)፤
9ኛ. ቀበና መካነ ሕይወት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤ.ክ.፤
10ኛ. ገነተ ኢየሱስ ገነተ ማርያም ቤ.ክ.፤
11ኛ. አንቀጸ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ቤ.ክ.፤
12ኛ. ፈለገ ሰላም ቤላ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ እና አቡተ ተክለሃይማኖት ቤ/ክ (ቀበና 18 ፓርክ አጠገብ)፡፡
/በፍኖተ ሕይወት ሰ.ት.ቤት ሚድያና ሕዝብ ግንኙነት ዋና ማስተባበሪያ ክፍል የተዘጋጀ።/
@Nigatu5
@Nigatu5
@Nigatu5
BY EOTC ቤተ መጻሕፍት
Share with your friend now:
tgoop.com/EotcLibilery/15438