tgoop.com/TIBEBnegni/2540
Last Update:
በጥቂቱ መታመን
መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ "በጥቂቱ ታምነሃል በብዙ እሾምሃለሁ!.." ማቴ 25፥21፡፡ ይህም ማለት በምድራዊ ነገሮች ላይ ታማኝ ሆነህ ስትገኝ በሰማያዊ ነገሮች ላይ እሾምሃለሁ ማለት ነው፡፡ በዚኛው ዓለም ታማኝ ሆነ ከቆየህ በዘለዓለማዊነት ውስጥ እሾምሃለው ማለት ነው፡፡ ይህ መመሪያ በብዙ መስኮች ላይ ተግባራዊ ሊሆን ይችላል... ዘመዶችህን በመውደድ ላይ ታማኝ ሆነህ ከተገኘህ እግዚአብሔር ጠላቶችህንም በመውደድ ላይ ይሾምሃል፡፡ ጠላትህን የምትወድበት ጸጋ ያድልሃል ማለት ነው፡፡
በትርፍ ጊዜዎችህ እግዚአብሔርን የምታገለግል ከሆንህ በሕይወትህ ጊዜ ሙሉ በእርሱ ላይ ትኩረት የምታደርግበትን ፍቅር ያድልሃል፡፡ የፈቃድ ኃጢአቶችን ከአንተ በማስወገድ ላይ ታማኝ ሆነህ ከተገኘህ እግዚአብሔር ያለ ፈቃድ ከሚመጡ ኃጢአቶች ነጻ ያወጣሃል፡፡
ንቁ ኅሊናህን ከክፉ አሳቦች የምትጠብቅ ከሆንህ እግዚአብሔር ንቁ ያልሆነው ኅሊናህን ንጽሕና ያድልሃል፤ ከዚህ በተጨማሪ የህልሞችህን ንጽሕናም ያድልሃል፡፡ ልጅ እያለህ ታማኝ ከሆንህ እግዚአብሔር ውጊያዎች በሚበዙበት በወጣትነትህ ዘመን ውስጥም ታማኝነትን ያድልሃል ሌሎች ሰዎች ላይ በቃላት ብቻ የማትፈርድባቸው ሆነህ በመገኘትህ ታማኝ ከሆንህ ይበልጥ አስቸጋሪ በሆነው በአሳብ እንዳትፈርድባቸው ያስችልሃል፡፡ ልክ እንደዚሁ ራስህን ከውጫዊ ንዴት በመጠበቅ ላይ ታማኝ ሆነህ ከተገኘህ እግዚአብሔር አውስጣዊ ቁጣ፣ንዴትና ቅናት ነጻ ያወጣሃል፡፡
በተለመዱ መንፈሳዊነቶች (በመንፈስ ፍሬዎች) ላይ ታማኝ ሆነህ ከተገኘህ እግዚአብሔር የመንፈስ ስጦታዎችን ያድልሃል፤ በመጀመሪያው ላይ ታማኝ ሆነህ ካልተገኘህ ሁለተኛውን ፈጽመህ ልታገኘው አትችልምና፡፡
እግዚአብሔር በመጀመሪያ የሚፈትሽህ በጥቂት ነገር ነው፡፡ በዚህች በጥቂቷ ነገር ላይ ታማኝ መሆንህ ካረጋገጥህ እርሱ በሚበልጠው ነገር ላይ ይሾምሃል፡፡ ውድቀትህንና አለመታመንህን በጥቂቷ ነገር ላይ ከገለጽህ ግን እግዚአብሔር በሚበልጠው ነገር ላይ አይሾምህም፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላልና፦ "ከእረኞች ጋር በሮጥህ ጊዜ እነርሱህ ቢደክሙህ ከፈረሶች ጋር መታገል እንዴት ትችላለህ?" ኤር 12፥5 ብዙ ሰዎች ዝቅተኛውን ኃላፊነት መወጣት ሳይችሉ ከፍተኛውን ኃላፊነት ለመቀበል ማሰባቸው እጅግ አስደናቂ ነገር ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች በተሰጣቸው ጸጋ ሳይጠቀሙ ተጨማሪ ጸጋ እንዲሰጣቸው የሚጠይቁ ናቸው፡፡ ይህን ሲያደርጉም "በጥቂቱ ታምነሃል፤ በብዙ እሾምሃለሁ" የሚለውን የእግዚአብሔር ቃል በመዘንጋት ነው፡፡
"መንፈሳዊ ቃላትና ጥቅማቸው" ከሚለው #አያሌው_ዘኢየሱስ ከተረጎመው #የብጹዕ_አቡነ_ሽኖዳ መጽሐፍ
💙💙🌿💙🌿💙🌿💙
@TIBEBnegni
BY ሰው መሆን...
Share with your friend now:
tgoop.com/TIBEBnegni/2540