tgoop.com/bemaledanek/2366
Last Update:
2• ንስሐ
2.5• ንስሐ መቼ መቼ እንግባ ?
ክፍል - ፱
✞ ከትንሹ ወደ ትልቁ መሰብሰብ ✞
ልዑል እግዚአብሔር ተፈጥሮአዊ ዑደትን በጠበቀ አሠራሩ በአብዛኛው ጊዜ ነገሮችን ሲገነባ ከትንሹ ወደ ትልቁ በመሰብሰብ የመመሥረቱ ጉዳይ እሙን ነው፡፡ ትልልቅ ነገሮች የተገነቡበትን መድረሻ ፈለግ ተከትለን ወደ መነሻቸው ብንሄድ፤ የምናገኘው ትንንሽ ነገሮችን ነው፡፡ እኛም የሰው ልጆች በዘፈጥረታቱ ስድስት ቀናት (ባሕሪያት) ድምርነት የተገነባን ፍጡሮች ነን፡፡
ከትንሹ ወደ ትልቁ የመሰብሰብ አሠራር ደግሞ የራሱ የሆነ ልዩ ጊዜ ወይንም ሂደት ይኖረዋል፡፡ መንፈሳዊ ሕይወትም ሂደት ነው፡፡ የምንነጋገርበት የንስሐ ጉዳይም እንዲሁ መነሻና መድረሻ ያለው ጉዞ እንዳለው ባለፉት ክፍሎች አንስተናል፡፡ ሁሉን መንፈሳዊ ሂደት ስለሚጠቀልለው ጉዞ የሐዲስ ኪዳን መጽሐፍ እንዲህ ይላል፦
"እኔ ክርስቶስን እንደምመስል እኔን ምሰሉ።" (1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 11፥1)
በመግቢያው አንቀጽ ላይ ማሳያ እንዳደረግነው የሰው ልጆች በስድስቱ ቀናት በተሰበሰበ የባሕሪይ ውጤትነት ተፈጥረናል፡፡ ከኛ አስቀድሞ የተፈጠሩት ፍጥረታት ባሕሪይ በሙሉ በኛ ውስጥ አለ፡፡ እነዚህን የተለያየ ስብጥር ያላቸውን ባሕሪያት ሥርዓት ባለው ደንብና ቅርጽ ለማስተዳደር እንድንችል ደግሞ የአምላክ መለኮታዊ ባሕሪይ በእፍታ በኩል ተለግሶናል፡፡ "ምድርን ግዙአት" የሚለው የገነቱ ድምፅ የተደመጠው ለዚህ ባሕሪያችን ነው፡፡ በሌላ አነጋገር በውስጣችን ያሉትን ባሕሪያት የመግዛት ሥልጣን የተጻፈልን በነፍሳችን ላይ ነው፡፡
ይህች ነፍስ የእግዚአብሔር መንፈሳዊ አካል እንደመሆኗ፤ በአርአያውና በአምሳሉ እንድንቀረጽ መልክ ሆና የተቀመጠች ሕልውናችን ናት፡፡ በገጠመን ውድቀትም የተነሣ ጀርባችንን ለእግዚአብሔር ሰጥተን ፊታችንን ወደ ምድር በማዞር ከፀሐይ በታች ወዳለው ሕይወት ስንሰደድ (በመጽሐፍ አገላለጽ ወደ አፈር ተመለሱ ስንባል)፤ ካጣናቸው (ከረሳናቸው) እውነታዎች መካከል አንዱ የአምላክ ምሳሌ ሆነን የተፈጠርንበትን የባሕርይ ልዕልና ነው፡፡
አዳም ፊቱን ወደ ምድር አዙሮ ከአምላክ ፈቃድ ወደ ሥጋ ፈቃድ ሲወጣ፤ ስድስቱ የቀን ባሕሪያት በውሰጡ ተሰብስበው እንደሠሩት ዘንግቷቸዋል፡፡ ወይንም ከስድስተኛው ቀን (ሰብአዊነት) እየፈረሰ በመውረድ ወደ አንደኛው ቀን (አፈርነት) ይመለሳል፡፡ ከትልቁ ወደ ትንሹ መመለስ እንደማለት!
ከትልቁ ወርደን ወደ ትንሹ ሄደን ከወደቅን፤ ለመነሣት ከፈለግን ይህንኑ ሂደት መከተል ይኖርብናል፡፡ ማለትም ከመጀመሪያው ቀን የአፈርነት ባሕሪይ ተነሥተን ወደ ስድስተኛው ቀን ሰብአዊነታችን መገሥገሥ አለብን፡፡ ይሄንን በራሳችን ልናደርገው አንችልም፡፡ ሰለዚህ የእግዚአብሔር ልጅ የሰው ልጅ ሆኖ ወደኛ ይመጣ ዘንድ ግድ ሆነ፡፡ በመሆኑም ከአዳም (የመጀመሪያው ዘመን ትውልድ) እስከ ድንግል ማርያም (ስድስተኛው ዘመን ትውልድ) ድረስ በስድስቱ ቀናት በኩል ዳግም እየሰበሰበ በቃሉ ሲሠራን ቆየና፤ [በሰማይ] በተፈጠርንበት አርብ አጋማሽ ([በምድር] 5500ኛው ዘመን) ላይ ሲገነባን የቆየው ቃል ሥጋ ሆነ፡፡ የጠፋብን እግዚአብሔርን የመምሰል መልክ ስለመገኘቱም ማረጋገጫ የሚሆነው ሕያው ቃል "የሚወለደው ቅዱስ የእግዚአብሔር ልጅ ይባላል" በሚለው የገብርኤል ብሥራት ውስጥ ተደመጠ፡፡ (የሉቃስ ወንጌል 1፥35)
መድኃኒቱ በእግዚአብሔር ልጅነቱ በኩል ሁላችንን የእግዚአብሔር ልጆች ሊያደርገን ሰማያዊ ሥልጣንን ሲሰጠን፤ ከዙፏና የወረደቺው ነፍሳችን ወደ ቀደመ ክብሯ ተመለሰች ማለት እንችላለን፡፡ በሌላ አነጋገር በክርስቶስ መንገድነት እየተጓዝን ወደ ባሕሪይ ልዕልናችን የምንመለስበት ጉዞ ሐዲስ ኪዳን በተሰኘ የምሕረት ቃልኪዳን ተሰጥቶናል፡፡ ይህንን ነው እንግዲህ ሐዋሪያው "እኔ ክርስቶስን እንደምመስል እናንተንም እኔን ምሰሉ" ሲል ያሳሰበን፡፡
በክርስቶስ መንገድነት (በክርስትና) እየተጓዝን ነው ማለት ፊታችንን (ሕልውናችንን) ወደ እግዚአብሔር ፈቃድና እውነት አድርገን አምላክን ወደ መምሰል ሰማያዊ ማንነት እያደግን ነው ማለት ነው፡፡ ይሄንን ሂደት የሚቃወመው እባብ በዚህ ጊዜ ከፊታችን መጥቶ ይቆማል (በሰማያዊው ጊዜም ላይ አዳም እግዚአብሔር አስቦ ወዳዘጋጀለት ከፍታ (ሰባተኛዋ ቀን) እየሄደ ሳለ ነበረ እባቡ በአካሉ (በሔዋን) ፊት መጥቶ የቆመው)፡፡
ዲያቢሎስ እንደ አምላክ በመሆን የዓመፃ መሻቱ ውስጥ የአምላክን መለኮታዊ አሠራርና ድንቅ ጥበብ ለመኮረጅ በእጅጉ የሚጥር ቀናተኛ ፍጡር ነው (ዘንዶው ሴቲቱ ፊት ልጅዋን ሊበላ ይቆማል ያልነውን ካለፉት ክፍሎች አስታውስ)፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ከትንንሽ ነገሮች ወደ ትልልቅ ገጽታዎች የሚመጡ ግሩም ነገራትን ሲሠራ፤ ክፉው መንፈስም ትንንሽ ጥፋቶችን ወደ ትልልቅ ውድመቶች ሰብስቦ ግዙፍ የሆነ የታሪክ ጉዳትንና የትውልድ ቁስለትን ያስከትላል፡፡
ይሄ ማለት በክርስትና የእምነት ጎዳና ላይ (በሐዲስ ኪዳን) በሁለንተናችን ስንራመድ፤ እንደ ጥንቱ አዳም (እንደ ትውልድ ብሉይ ዘመን) ፊታችን ወደ ሥጋ ፈቃድ እንዲጠመዘዝ በየቀኑ ይታገላል፡፡ እነዚህ የየዕለት ፍልሚያዎቹ በዋነኝነት ኃጢአትን እንድንፈጽም በማስደረግ ላይ ያተኮሩ ናቸው፡፡
ክፉው መንፈስ ከሰውነት ውስጥ ገብቶም ይሁን ከውጪ ባለ ሁኔታ፤ ፈተናዎቹን የሚያመጣው "በየቀኑ" ነው፡፡ ምክንያት? .. ዘወትር የተለያዩ ስልቶችን እየተጠቀመ ዓመፃ ላይ እንድወድቅ ፈተነ ማለት፤ ከትንሹ ወደ ትልቁ በመሰብሰብ ዑደት የሚዞር የጊዜ ሥርዓትን ሳያባክን በሥራ ላይ በመዋል፤ ሲታዩ ትንንሽ "የሚመስሉ" አጋጣሚዎችን ሰብስቦ እያጠራቀመ በመዋጋት፤ በፍጻሜው ነፍስን ከእግዚአብሔር እቅፍ እስከወዲያኛው መለየት የሚል ትልቅ ራእዩን እየተከተለ ነው ማለት ስለሆነ፡፡
መናፍስት ጥፋትንና ኃጢአትን ወደ ሰው ልጆች ከማድረስ ጋር በተያያዘ ተልዕኮአቸው፤ ይሄ ትንሽ ፈተና ነው ብለው የሚንቁት፣ ይሄ ትንሽ ጽድቅ ነው ብለው የማይፋለሙት፣ ይሄ ትንሽ መሰናክል ነው ብለው የማያስቀምጡት፣ ይሄ ለውጥ የማያመጣ ትንሽ ትግል ነው ብለው የሚዘሉት፤ የየቀን አጋጣሚ የላቸውም፡፡ እንደው ምንም ዋጋ ባይኖረው እንኳ፤ የደቂቃ እምባ ማስለቀስ ለእነርሱ በእጅጉ ደስታን ይሰጣቸዋል (በቅዱሱ መንፈስ አንዲቱ በግ እስከ መስቀል ሞት ድረስ የተወደደችው በተቃራኒው መንፈስ በእጅጉ ስለተጠላች እንደሆነ ያስተውሏል!)፡፡
እኛ ደግሞ በተቃራኒው ትንንሽ ብለን የመጠን ልክ ያወጣንላቸውን ኃጢአቶች፣ ጥቃቅን የሚመስሉ ስሕተቶችንና የተላመዱንን ጥፋቶች እንንቃለን (ግን ክርስቶስ የማይደስበት ትንሽ ጽድቅ፥ ሰይጣን የማይደስትበት ትንሽ ኃጢአት የለም!)፡፡ ትንንሽ አልከናወን ያሉ ችግሮችን ይዘናቸው እንጓዛለን፡፡ በዚህም ርኩሳን መናፍስት ለሚገነቧቸው ትልልቅ ዓመፃዎች የግንባታ ጡብ የሆኑ ትንንሽ ልማዶች የማንታረምባቸው ዝንባሌዎቻችን ሆነው አንዴ በትልቁ የምንፈርስበት ምክንያት፤ ያላስተዋልናቸው አሊያ በቸልተኝነት የምናልፋቸው የየዕለት ውድቀቶቻችን ናቸው፡፡
ለምሳሌ፤ ሐሜት፣ ፌዘኝነት፣ ችኩልነት፣ ግንፍልነት፣ ግዴየለሽነትና መሰል ጠባያት በየቀን የኑሮ ልምምዳችን ውስጥ የጊዜያችን አካል ለመሆን የሚታጉሉ "ትንንሽ" የመናፍስት ፈተናዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ስሜትን ተገን ያደረጉ የዕለት ተዕለት ግፊቶች፤ በአብዛኞቻችን አኗኗር ውስጥ የተካተቱና በቁጥር እጅግ የበዛ ሰው ስለሚገኝባቸውም እንደ ጥፋት ከመቆጠር የራቁ አሰናካይ "ጠጠሮች" ሆነዋል፡፡
BY በማለዳ ንቁ ቁጥር ! ፪
Share with your friend now:
tgoop.com/bemaledanek/2366