tgoop.com/bemaledanek/2367
Last Update:
ከትንሹ ወደ ትልቁ በመስብሰብ ሂደት ውስጥ ብዙዎቻችን ከተጎዳንባቸው ነገራት መካከል አንደኛው ውሸት ነው፡፡ በየቀኑ ትናንሽ ውሸቶችን ቀለል አድርገን ስንዋሽ .. ስንዋሽ፤ እንግዲህ ዛሬ በዚህ ዘመን፥ በዚህ ትውልድ "የማይዋሽ ሰው" ውሸታም እስከሆነበት ጥግ ሁላችንም ሐሰትን የሕይወታችን ባለንጀራ ስናደርገው፤ እውነትን ብቻ እየተናገርን ያሳለፍናቸው ቀናት እየከሰሙ .. እየከሰሙ ሄዱ፡፡ ስለሆነም ከውሸት ጋር ተጣብቶ መኖርን ተላምደን (ከትንሹ ወደ ትልቁ የሚሰበሰቡ ነገራት ልማድ የመሆን ዕድላቸው በጣም ሰፊ ነው)፤ ንስሐ በተባለ ሽምግልና ከእውነት ጋር ታርቀን የመንፈስ ቅዱስ መግለጫዎች ለመሆን እስኪከብደን ድረስ በጣም ተቸገረን እንገኛለን፡፡
ባለንበት የሐዲስ ኪዳን ዘመን ዲያቢሎስ የየዕለት ኃጢአቶችን ለሕይወታችን ለማሰልጠን በእልህና በትጋት ጥርሱን ነክሶ የሚሠራው ለዚህ ነው፡፡ ከኃጢአት ጋር ተስማምቶ በመኖር ውስጥ፣ ዓለማዊ እውቀትን ብቻ እንደ ኑሮ መርህ ተላምዶ በመቆየት ውስጥ፣ ከሥጋዊ ጊዜያት የሚፈልቅ ዓመፃን እንደ ሕይወት ገጠመኝ በመቁጠር አስተሳሰብ ውስጥ፤ በመድኃኒቱ ከትንሹ ወደ ትልቁ በመሰብሰብ ድንቅ ሥራ በኩል የተካፈልነውን ሰማያዊ ልጅነት እንዳናሳድግ (እግዚአብሔርን እንዳንመሰል) በመታገል ወደ ብሉይ ዘመን ውድቀት ሊመልሰን ቀን ከሌት ሳይደክም ይለፋል፡፡ አየተሃል ወዳጄ? .. ለዘመናት ከትንንሽነት ተነሥተው በመደጋገማቸው ምክንያትነት የለመድካቸው የኃጢአት ጊዜያት ተሰብስበው ትልቅ የበደል ክምር ሲሆኑ፤ ይሄንን ክምር ለመደርመስ የሚወጣ የንስሐ ጉልበት አጠረህ፡፡ ያ ማለት በዘመነ ምሕረት ሳለህ ዓመተ ፍዳን ትቆጥራለህ ማለት ነው፡፡ ከትንሹ ወደ ትልቁ ምን ማለት? .. መሰብሰብ!
ስንት ውሸቶች እስከዛሬ ተሰብስበውብናል? ሰንት ዝሙቶች እስከዛሬ ተከማችተውብናል? ስንት የምቀኝነት ወቅቶችን እስከዛሬ አሳልፈናል? ስንት ጽድቅን የሚቃረኑ ቀናትን እስከዛሬ ኖረናል? ስንት የበደል ውጤት የተመዘገበባቸው ቆይታዎች እስከዛሬ ተገኝተውብናል? እስኪ በደንብ እናስብ! ዛሬ ወደ መንፈሳዊው ስፍራ ገብተን ጸንተን እንዳንኖር የሚታገሉ ስንት ትናንሽ ኃጢአቶች እስከዛሬ ተሰብስበው ትልቅ መሰናክል ሠርተው ይሆን?
የርዕሳችንን ጥያቄ የምንመልሰው እንግዲህ እዚህ ቦታ ላይ ይሆናል፡፡ ንስሐ መቼ መቼ እንግባ ከተባለ፤ በየቀኑ የሚል ቁርጥ መልስ መገኘት ይኖርበታል፡፡ ትናንሽ የዲያብሎስ ምሪቶች ተሰብስበው ትልቅ የጥፋት መድረሻ ላይ እንዳያስቀምጡን፤ ትናንሽ "የአጋጣሚ" ክፍተቶች ተሰብስበው ትልቅ የሕይወት ገደል እንዳይፈጥሩ፤ ትናንሽ የየዕለት ኃጢአቶች ተሰብስበው ትልቅ የንስሐ መጋረጃ እንዳይዘረጉ ሲባል፤ በየዕለቱ "አውቄም ሆነ ሳላውቅ የፈጸምኳቸውን ኃጢአቶች ሁሉ ይቅር በል" በሚል የልብ ጸሎት መበርታት ያስፈልገናል (በዘወትር ጸሎት ላይ "እኛ የበደሉንን ይቅር እንደምንል፥ አቤቱ በደላችንን ይቅር በለን" የምንለው ለዚህ ነው፤ ከልብ እንጸልየው!)፡፡
ብዙዎቻችን የየዕለት ኃጢአቶቻችንን በየዕለት ንስሐ አናጥባቸውም (የመጀመሪያ ምዕራፋችን ፍቅር ትዝ አለን፡፡ ፍቅር ቢኖረን ኖሮ..) ንስሐ ብዙ ጊዜ ስንገባ የምንገኘው ኃጢአቶቻችን "ከተጠራቀሙ በኋላ" ነው፡፡ በዘወትር የንስሐ ጸሎትና በተደጋጋሚ የንስሐ ስግደት፤ ትንንሽ የሚመስሉ ኃጢአቶችን ከሥር ከሥሩ አንሰርዛቸውም፡፡ በዚህም በየዕለቱ የሚከማቹ በደሎች፣ ስሕተቶችና ክፉ ጊዜዎች ራሳቸውን በመደጋገም አካሄድ ውስጥ ተላምደውን፤ ለዲያቢሎስ የእስራት ገመድ ማጥበቂያ እየሆኑ እንዳለ አልገባንም፡፡
ዲያቢሎስ ለዘመናት ሕይወታችን ውስጥ አድፍጦ ቆይቶ፤ ባልተሰረዩ የየዕለት ነጠላ ኃጢአቶች በኩል ያገኘውን ኃይል፤ እነዚህ ትናንሽ ኃጢአቶች ተሰብስበው ትልቅ ውድቀት እንዲሆኑ ለዓመታት የለፋበትን ኃጢአትን የመደጋገም ሥራው፤ እንደገናም ወደፊት ሊያከናውናቸው ያቀዳቸውን የኃጢአት ጊዜዎች፤ ከንቱ ሆነው እንዳይቀሩበት በጥብቅ ስለሚፈልግ በየቀኑ በንስሐ መንፈስ እንዳንመላለስ ይፋለማል፡፡ ይቅር ባይነትና ይቅርታ ጠያቂነት አማናዊ መሥዋዕት ናቸውና፥ እነዚሀን ያስቀራል፡፡ በሌላ አገላለጽ ከልጅነት አንስቶ፤ ጥፋትን በመደጋገም፣ ኃጢአትን በማስለመድ፣ ከእግዚአብሔር የራቀ ሕይወትን የኑሮ አካል ለማድረግ የተጓዘባቸው ከትንሹ ወደ ትልቁ የመሰብሰብ ሂደቱ በቀላሉ እንዲከሽፍበት ፈጽሞ አይፈልግም፡፡ ስለሆነ የተጠመጠመውን በመፍታት ቆይታ ውስጥ (ነቅተህበት እየታገልከው ሳለ)፤ ነገ ተስፋ ልትቆርጥ እንደምትችል እያሰበ ዛሬን ይታገልሃል (ተስፋ የሌለው ተስፋ አድራጊ!)፡፡
በመሆኑም፤ የየዕለት ንሰሐዎችን፣ የጸሎት ጊዜዎችን፣ የሰግደት ቆይታዎችን፣ የመቀደስ ልምምዶችን በማከናወን፤ እኛ ደግሞ ከጠላታችን አቅጣጫ በተቃራኒው ተጉዘን፤ ትናንሽ ጽድቆችን፣ ትናንሽ ቅድስናዎችን፣ ትንንሽ የአምልኮት ሰዓቶችን በመስብሰብ፤ በትልቁ እየተገለጠ የሚሄድ ከእግዚአብሔር ጋር የመገኘት አኗኗርን ለመኖር ቁርጠኛ አቋም ልንይዝ ያስፈልገናል፡፡
በአጀማመራችን አካሄድ ለመጨረስ ያህል፤ ወደ አፈርነት እየተመለስን በሞት ቁጥጥር ሥር ውለን የነበርነው የሰው ልጆች፥ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ሞትን የምናሸንፍበት የባሕርይ አለኝታነት ሲሰጠን፤ ይህንን ስጦታ ጠብቀን ለመጓዝ የምንችለው በንስሐ ሕይወት ስንደገፍ ነው፡፡ የሥጋ ድክመት፣ እንደጋራ የተላመድነው ዓላማዊ አኗኗር እና ከነዚህ ጀርባ ሆነው የሚንቀሳቀሱ ክፉ መናፍስት እግዚአብሔርን ወደ መምሰል ታላቅ የቅድስና ተራራ እንዳንወጣ በየሰዓቱ በኃጢአት መዳፍ ስበው ቢጎትቱንም፤ ከተጎተትንበት ነጥብ ላይ ቀጥለን ወደ ሉዓላዊ ክርስትና እስክንደርስ ድረስ ምርኩዝ ሆኖ የሚያግዘን የአምላክ ክንድ ንስሐ ይባላል፡፡ "ዘወትር" እንጠቀምበት!
-------------------
ንስሐ እንዲህ እንዲህ እያለ እዚህ አድርሶናል፡፡ ወደ ቅዱስ ቁርባን ምዕራፍ መጀመሪያ ላይ ስንደርስ "በሉ በርቱ" ብሎ ተለይቶናል (እናመሰግናለን!)፡፡ የእኛም የሰማያዊው ማዕድ ጉዞአችን ይቀጥላል፡፡ ከአጠገባችን "ፍቅር" ስላለ ካሰብንበት እንደምንደርስ አንጠራጠርም፡፡ ስንጨርስም ፍቅር በዖሜጋነቱ መድረሻ ላይ ሆኖ እንደሚቀበለን እናምናለን፥ አምነንም እንኖራለን፡፡ አስጀምሮ ላስፈጸመን ለይቅር ባዩ አምላክ ምስጋና ይግባው፡፡
ወደ ሥጋና ደሙ መጓዛችንን እንቀጥላለን. . .
#ጸባኦት_ይከተላችሁ
@bemaledanek
BY በማለዳ ንቁ ቁጥር ! ፪
Share with your friend now:
tgoop.com/bemaledanek/2367