tgoop.com/bemaledanek/2426
Last Update:
አንባቢ ተረድተኸኛል?.. በኃጢአተ አዳም ጀምሮ በተለያዩ ዘመናት ላይ ተጨማሪ ኃጢአቶችን በማስፈጸም ፥ ሕገ ኦሪትን በማስጣስና ጽድቅን ከሰው ባሕሪይ በማሸሽ፤ ብዙ ነፍሳትን ሰብስቦ እየዋጠ እባቡ ፋፍቶ ዘንዶ መሆን ችሎአል፡፡ ነገር ግን ክርስቶስ የዚህን ከይሲ ክፋት ሊያስወግድ በሥጋ የተገለጠ መሢሕ ሲሆን በመስቀሉ ኃይል የጥፋቱን ሥራ ከሰዎች ላይ ጠርቆ አስወግዶ፤ ለኃጢአቶች ሁሉ መፍለቂያ የሆነቺውን የአዳምን በደል በመካስ ከታሰርንበት እንድንፈታ አድርጎናል፡፡ ዳሩ ግን ሰዎች ከተጣባቸው ክፉ ዘር ተላቅቀው እንደገና አዲስ ፍጥረት የሚሆኑበትን ኪዳን ሊያምኑበትና ሊቀበሉት አልፈቀዱም፡፡ ስለዚህ በመድኃኒታችን ሰይፍ ለሞት የታረደቺው የአውሬው ራስ ተፈውሳ ልትገለጽ ተቻላት፡፡ ኃጢአተ አዳም እንደገና ልትተገበር በቃች፡፡ እስቲ ወደ ሀገራችን እንምጣ..
ከታሪክ ማኅደራችን እንደተቀመጠው ሀገራችን ኢትዮጲያ ይፋዊ በሆነ መልኩ በሐዲስ ኪዳን አምና ወደ ክርስትናው የመጣቺው በ328ዓ.ም በአክሱም ዘመነ መንግሥት እንደሆነ ይታወቃል፡፡ መዳንን ማምጣት ያልቻለው የብሉዩ ሕግ በሐዲሱ ተፈጽሞ፥ ኢትዮጲያም ከዚህ በእግዚአብሔር ልጅ መምጣት ምክንያት ከተገለጠው ብርሃን ተካፋይ መሆን ችላለች፡፡ በሌላ አገላለጽ የክፋት መናፍስት አገዛዝ ተሽሮ፥ በክርስቶስ ስሙ ያመነቺውና የተቀበለቺው ሀገራችን የዘንዶውን ራስ የምትቀጠቅጥበትን የሃይማኖት መዶሻ (የተዋሕዶ ዶግማ) ተቀብላለች፡፡ ሥርዓተ መንግሥቷን፣ መተዳደሪያ ሰነዷን፣ ባሕሏን፣ አኗኗሯን፣ ዕውቀቶቿን፣ .. ሁሉ በክርስትናው መንፈስ እንዲቃኙ በመትጋት ሁለንተናዊ ማንነቷን ሐዲስ አድርጋ መንቀሳቀስ ጀምራለች፡፡ ጽድቅና ኩነኔ የማኅበረሰብ ብያኔዎች ማጥሊያዎች ሆኑ፡፡ ትክክልና ስሕተት በቅድስና ሚዛን እንዲለኩ መሥፈሪያ ተሰጣቸው፡፡ መንፈሳዊ እውነቶች የፖለቲካ መዋቅሩን እንዲመሩ ተደረገ፡፡ "ቀድሞ የነበረው አውሬ አሁን የለም" ማለቱን ያስታውሷል፡፡
"የለም" ሲባል ደብዛው ጠፍቷል በሚል እሳቦት እንዳይተረጎም ለአንባቢ አሳስባለሁ፡፡ ሰይጣን የማይኖርበት ጊዜ የለም፡፡ በሌላ አነጋገር በማይቻል ሁኔታም ይሁን የሚቻለውን ያህል ከመሥራት አያርፍም፡፡ ከክርስቶስ መሰቀል በኋላ እውነትን የማሳደዱ አዋጅ እንዳልቆመ ልብ እንላለን፡፡ መቃብሩ ላይ ጠባቂዎችን በመሾም የትንሣኤውን ምስክርነት እንዲያሳብሉ በአይሁዳውያኑ በኩል ሲጠነስስ መገኘቱ ላነሳነው ጭብጥ ምሳሌ ነው፡፡ ከትንሣኤውም በኋላ የጌታን ደቀመዛሙርት ሲያንከራትትና ሲያስገድል የሚታየውም ለዚህ ነበር፡፡ ወደ ኢትዮጲያው ጉዳይ ስንመለስ፥ ክርስትናው ወደ ሀገሪቱ በመግባቱና ሀገሪቱም ሥር ነቀል በሚያሰኝ ለውጥ በእውነት ወንጌል በመጠመቋ ዲያቢሎስ ይፋዊ ሥራውን ከመከወን ተወግዶ ነበር፡፡ ሆኖም በውስጥ መስመር እውነት እንዳይስፋፋ ሲሸርብ፥ በአንጻሩ ይመለኩ የነበሩ ባዕድ አምልኮቶች እንዲስፋፉ ሲደክም ቆይቷል፡፡ ምእመናንን በተለያየ መልኩ ሲፈትንና ሲያሳሳት መክረሙ የታሪክ ክስተቶችን በማጥናት በቀላሉ ማወቅ ይቻላል፡፡ ዘመን መጥቶለት ዓላማው ሙሉ ለሙሉ ግቡን እስኪመታለት ድረስ ድምፅ አጥፍቶ በጥንቃቄ ይንቀሳቀስ ነበር፡፡
እነሆ፥ ሲያልመው የኖረውም አልቀረ ይፋ የሚወጣበት ጊዜ ደረሰለት፡፡ ከአንድ ሺሕ ስድስት መቶ ዓመታት በኋላ ሀገረ እግዚአብሔር በሚል ቅጽል ስትጠራ በኖረች ምድር ላይ "እግዜር የለም" የሚል አብዮተኛ ትውልድ ተነሣ፡፡ ሃይማኖትን ከሚክድና መንፈሳዊ ዓለምን ከሚንድ ወገን የተማሩ "ምሁሮች" የ60'ዎቹን ዘመን አብዮት አቀጣጠሉ፡፡ "ሶሻሊዝም ይለምልም፥ ፊውዳሊዝም ይወድም" ሲሉ በየአደባባዩ ጮኹ፡፡ እግዜር መረጠኝ የሚለው የንጉሣዊያኑ ሥርዓትና አስተዳደር፥ ሀገሪቱን ለድንቁርና ብሎም ለድህነት እንዳጋለጣት ደረስንበት አሉ፡፡ ስለዚህ በማርኪሲዝም ቁሳዊ ዓለምን በሚያበረታታ ርዕዮት ችግራችንን "እንቀርፋለን" በማለት፥ ቀደም ሲል ሀገሪቱ ለሺሕ ዓመታት ስትመራበት የነበረውን ሥርዓት እያከታተሉ ማጥፋትን ሥራቸው አደረጉ፡፡ ጥፋትና ልማት የሚለዩበትን አፍታ ሳይወስዱ፥ በነበረው ታሪክ ላይ እንደወረደ ዓመፁ፡፡ ወልደው ያሳደጓቸውን አባቶች፣ ዕሴቶች፣ ሕብረተሰባዊ ደንቦች፣ መንፈሳዊ መርሆች ለታሪክ እንኳ እንዳይቀመጡ አንድ ጊዜ ዘመቱባቸው፡፡ አንባቢ አሁን ምን ገባህ?.. "አውሬው አስቀድሞ እንደነበረ አሁንም እንደሌለ፥ ነገር ግን እንዳለ ሲያዩ.." የሚልህ አልገባህም?
ኃጢአተ አዳም "እንደ አምላክ በመሆን ከንቱ ምኞት" የተፈጸመች ኃጢአት ናት፡፡ ምክሩንም ያቀበለው ቀድሞ "አምላክ እኔ ነኝ" ሲል ያመፀው እባብ ነበር፡፡ የሰው ልጅ እንደ አምላክ እሆናለሁ ሲል አምላክ የለምንም እየተናገራት እንደሆነ ያስተውሏል፡፡ የኛዎቹ፥ የ1960'ዎቹ አብዮተኞች "አምላክ የለም" በሚል የማርኪሲዚም እባብ-ፍልስፍና የተደነፉ ሶሻሊስቶች እንደሆኑ ይታወቃል፡፡ የክሕደቱን ፍልስፍና ካጠኑት በኋላ እንደ ማሳያ የሆነላቸውን የሶቪየት ሕብረትን "ብልጽግና" ሲያዩ የማርኪሲዝሙ ሕብረተሰባዊነት ጥበብ ሰጪ፥ ፖለቲካዊ ሥርዓትም አድርጎ ለመጠቀም የሚያጓጓ ሆነባቸው፡፡ (ኦሪት ዘፍጥረት 3፥6) አላመነቱም! "ኢትዮጲያዊ" ማኒፌሶቶአቸውን ከቀዱት የሶሻሊዝሙ ዕውቀት ላይ በማስደገፍ በ1968 የሀገሪቱ ሥልጣን ላይ ወጡ፡፡ ከዛፉ ፍሬ የገመጡለት የዛ ጊዜው ዘንዶም እየተጎተተ መጥቶ ወንበራቸው ላይ ተደላደለ፡፡
ዘንዶው ፖለቲካዊ ኃይልን ከእጁ እንዳስገባ ሲያይም፥ በሐዲስ ኪዳን መነሻዎቹ ዓመታት ክርስትናን በይፋ ሲያሳድዱ እንደነበሩት ሮማውያን ነገሥታት፥ መንፈሳዊነትን ለማጥፋት ብቀላ ባለበት እልህ ሠራዊት ያስከትት ጀመር፡፡ በእርግጥም ከ50 ዓመታት ወዲህ የሆነብንንና የተነሣውን ትውልድ እናውቃለን፡፡
መድኃኒታችን ከግምጃ ቤት አጠገብ በመቅደስ ሆኖ ያስተምራል፤ አይሁዳውያኑ ይሰሙታል፡፡ በሚናገራቸውም ግር እየተሰኙ ይጠይቁታል፥ እርሱም ይመልሳል፡፡ የሚናገራቸውንም እየሰሙ ከአይሁዳውያኑ ውስጥ የሚያምኑበት ሰዎች እየበዙ መጡ፡፡ እርሱም እንደ እውነትነቱ ከባርነት ነጻ የሚያወጣው መሢሕ እንደሆነ ይገልጽላቸዋል፡፡ ይሄን ጊዜ ያመኑቱ ሳይቀሩ ቁጣ ይጀምራሉ፡፡ "እኛ የአብርሃም ዘር ሳለን እንደባሪያዎች አርነት ላውጣችሁ ትላለህን?" አሉት፡፡ እርሱም መልሶ የኃጢአት ባሪያዎች እንደሆኑና በእርሱ ካልሆነ ከዚህ ባርነት ነጻ ሆነው የእግዚአብሔርን ልጅነት እንደማያገኙ ዕንቅጩን ይነግራቸዋል፡፡ እነርሱም የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆኑ ሲነግሩትና በንግግሩም ሊገድሉት እንደሚፈልጉ ባስተዋላቸው ጊዜ የሚከተለውን ይላቸዋል፦
"እግዚአብሔርስ አባታችሁ ከሆነ በወደዳችሁኝ ነበር፤ እኔ ከእግዚአብሔር ወጥቼ መጥቻለሁና፤ እርሱ ላከኝ እንጂ ከራሴ አልመጣሁምና። ንግግሬን የማታስተውሉ ስለ ምንድር ነው? ቃሌን ልትሰሙ ስለማትችሉ ነው። እናንተ ከአባታችሁ ከዲያብሎስ ናችሁ የአባታችሁንም ምኞት ልታደርጉ ትወዳላችሁ።"
(የዮሐንስ ወንጌል 8፥42-44)
ሰዎቹ የእግዚአብሔር ልጅ ነን ቢሉም አባታቸው ሌላ ነበር፡፡ ዲያቢሎስ! ይሄ የሐሰት አባት የነርሱም አባት ሲሆናቸው በዘርነት አብሯቸው ያለ ጭምር ስለመሆኑ እንገነዘባለን፡፡ ከዝሙት አልተወለድንም ቢሉም፥ ባልተሠረየ ኃጢአት ውስጥ የሚዋለዱበት ሥጋዊ ሥርዓት ለክፉው መዋረስ የተመቸ ነበር፡፡
BY በማለዳ ንቁ ቁጥር ! ፪
Share with your friend now:
tgoop.com/bemaledanek/2426