tgoop.com/bemaledanek/2752
Last Update:
እውነቱ ይህ ሆኖ ሳለ እንኪያስ ለምንድነው ምእመናን ከቅዱስ ቁርባን የተለዩት? ከክርስቶስ ማዕድ መካፈል ያቃተቸው ክርስቲያኖች ስለምን በርካታ ሆኑ? አዲስ ኪዳንን የምሕረት ዘመን ያሰኘው የመዳን ዋስትናችን የመስቀሉ መሥዋዕት ሆኖ እያለ ብዙዎች ከእርሱ ለምን ራቁ? የተዋሕዶ ሃይማኖት አንዱ ዓምድ (ዶግማ) የበጉ ሥጋና ደም ነው መባሉ በአማኞች ሕይወት ላይ ለምን በተጨባጭ አልተተረጎመም?.. ?
የነዚህና መሰል ጥያቄዎች ቀጥተኛ መልስ በመነሻ አንቀጻችን ላይ የተጻፈው ይሆናል፡፡ እንደ እግዚአብሔር ለመሆን ያለማቋረጥ የሚጥረው ዲያቢሎስ፥ አትንኩት ብሎ በዐዋጅ እንዲከለከሉ ካደረጋቸው ገደቦች መካከል መቀደስ (ቀ ጠብቆ ይነበብ) በግንባር ቀደምነት ይጠቀሳል፡፡
ስናስታውስ፥ በመጀመሪያ በእኛ በእግዚአብሔር መካከል "አትብሉ"ን አሰበልቶ ከፈቃዱ ነጥሎን ነበር፡፡ አሁንም ይሄው አካሄዱ ይዘቱን ሳይለውጥ ቀጠለና "ብሉ" የተባለውን አትብሉ አስደርጎ ፈቃዱን እንዳንኖር እየተዋጋን ይገኛል፡፡ የተከለከልነውን አስፈቅዶ፥ የተፈቀደልንን ከልክሎናል፡፡
አንባቢ የምለውን ተመልከት፥ በነገሩ ላይ ጌታ ማስተዋልን ይስጥህ! ክፉው መንፈስ እንደ ፍላጎቱ በሰውነታችን ላይ ፈላጭ ቆራጭ እንዲሆን እኛነታችንን ከመንፈስ ቅዱስ መለያየት ያስፈልገዋል፡፡ በቃ ቅዱስ ቁርባን ላይ ከተለያየ አቅጣጫ የተከፈተው አጠቃላይ ዘመቻ ከዚህ የጠላት ፍላጎት ይመነጫል፡፡ ከእግዚአብሔር በራቅን ልክ እርሱ ወደኛ የሚጠጋበት ርቀት ያጥርለታልና፥ ከአምላክ ጋር የሚያስተባብረንን የኪዳኑን ጸጋ እንዳናገኘው ባገኘውና በሆነለት መንገድ ሁሉ እየተጠቀመ ያሸሸናል፡፡ እንዴት?
3.3.1. በኃጢአት በኩል
ኃጢአት በሰውና በአምላክ መካከል ያለ የዓመፅ ግድግዳ ነው፡፡ ከእግዚአብሔር እንዳንሆን የሚፈልገው መንፈስ፥ ኃጢአትን በማስተዋወቅ፣ በማስፈጸምና በመምራት ከመለኮት ንጽሕና ይለያየናል፡፡ ብቻ ሳይሆን፥ ኃጢአት ከሕይወታችን ሳይወጣ እንዲቆይ በማጽናት ቅድሰና እንዳያገኘን ነቅቶ ይጠብቃል፡፡
የመድኃኒታችን ሥጋና ደም ስለ ኃጢአት ሥርየት የተሠዋ ዘላለማዊ መሥዋዕት እንደሆነ በክፍል ፫ አይተናል፡፡ እነሆም ዲያቢሎስ በኃጢአት ረግረግ ተውጠን እንድንያዝ ሲወድ፥ ኃጢአትን ከሥር መሠረቱ ነቅሎ የሚጥለውን ቅዱስ ቁርባን በእጅጉ ይጠላዋል፤ ይፈራዋል፡፡ ይሄንን ፍራቻውንም ባላጋራ ሆኖ ላደረበት አስተሳሰባችን ለማጋባት የሚከተሉትን ሁለት ዋና ዋና ስልቶች አቀናጅቶ ይተገብራል፡፡ እንመልከታቸው፡፡
1• ከኃጢአት የመላቀቅ ፍራቻ
"እኔ ኃጢአተኛ ነኝ፤ ለሥጋና ደሙ የበቃሁ አይደለሁም፤.. " የሚሉ ዓይነት ምላሾች፥ ቅዱስ ቁርባን ለምን እንደማይወስዱ ከተጠየቁ ብዙ ምእመናን ዘንድ ይነገራሉ፡፡ እነዚህ ንግግሮች በአብዛኛው ሰማያዊውን አምኃ ከማክበርና ከመፍራት የተነሱ እንደሆነ ይታሰባል፡፡ በእርግጥስ፥ ከኢየሱስ ክርስቶስ መለኮታዊ አካል የሚያካፍለን ክቡር ሥጋና ክቡር ደም እንደምን ያለ የክብር ጥግ፣ እንዴት ያለ የፍርሃት መጨረሻ ቢቸረው (ቸ ጠብቆ ይነበብ) ይመጥነው ይሁን?
ነገር ግን መላእክት፣ ቅዱሳን እና ቀደም ሲል እምነታቸውን በየዋህነትና በፍቅር ሲኖሯት የነበሩት ሁሉ ለቅዱሱ መሥዋዕት የሰጡት የክብር ፍራቻ፥ ለዛሬዎቹ እኛ፥ ከኃጢአት ሳይርቁ የመኖር ፍራቻን የምናለባብስበት መጋረጃ ሆኖ ነው እያገለገለ ያለው፡፡ የአብዛኞቻችን "ለክርስቶስ ሥጋና ደም አልገባም" (ገ ጠብቆ ይነበብ) ከምትለዋ የትሕትና ንግግር ጀርባ፥ ኃጢአትን የለመደ ሽሽግ ማንነት አለ፡፡
በሥጋዊቷ ዓለም ስንኖር ክፋቶች ክፉነታቸው እንዳይገለጥልን፥
ቢገለጥልንም ከክፋቶች እንዳንመለስ ማድረግ የክፉ መናፍስት ቀንደኛ ሥራ ነው፡፡ ይኸውም ከእግዚአብሔር የሆነ ቅዱስ ዕውቀት በማሳጣትና ኃጢአትን ተላምደን እንድንኖር ሁለንተናችንን በማጠር የሚከውኑት ይሆናል፡፡ ስለ ኃጢአትና የኃጢአት ራስ ዲያቢሎስ ደገኛ ትምህርት ካለማግኘታችን ጋር ተያይዞ፥ ዓለም በዘመናት ሂደት ሰብስባ ባጠራቀመቺው የአስተሳሰብ ሥርዓት እንድንቀረጽ እየሆነ ከልጅነታችን እናድጋለን፡፡
ይሄ አስተዳደጋችን ደግሞ፤ ጠባይን፣ ፍላጎትን፣ ውሳኔንና ዓላማን ሁሉ በተጽዕኖ የሚነካ፥ ከሕይወታችን ጋር ተጋብቶ ያለ የማንነት መገለጫችን ይሆናል፡፡ ክፉው ለዚህ አስተዳደጋችን ነው እንግዲህ ኃጢአትን በተለያየ ዕውቀት በኩል ለአመለካከታችን በመመገብ፥ ዓመፃዎችን ከለጋነት የሚያለማምደን፡፡ [ወጣቶች፥] ኋላችሁን አስቡት እስኪ፡፡ እስከ አሁናችሁ ድረስ ያወቃችኋቸውና የለመዳችኋቸው ነገራት ምንድን ናቸው? ለጽድቅ ያላቸው ቅርበት ለኃጢአት ያላቸው ርቅትስ ምን ይመስላል?..
ምእመናን ከኃጢአት ጋር ተዛምደው የኖሩባቸው የዕድሜ ቆይታዎች ወደ ተቀደሰው መብል እንዳይመጡ የሚጠልፉ ዕንቅፋቶች ናቸው፡፡ ትናንትናችን ተሳስሮት የቆየው የልምድ ኑሮ ለውጥን አፍኖ የሚይዝ የክፉ መንፈስ ጥምጣም ነው፡፡ ለረጅም ጊዜያት ከውስጣችን ሲገነባ የቆየን ካብ ማፍረስ ራሱን የቻለ ጣር አለበት፡፡ ለምሳሌ ሐሜት ዕለት ተዕለታችን የሆነብን ሰዎች ከቅዱስ ቁርባን በኋላ ያሉት ቀኖቻችንን ምን እንደሚያወሩ ከወዲሁ ስለምናውቅ "የበቃሁ አይደለሁም" በሚል ቋንቋ ሸፍነን "ልምዴን የምተው አይደለሁም" የምትል የውስጠታችንን መልእክት እንተነፍሳለን፡፡ ዝሙት፣ ስካር፣ ዳንኪራ፣ ጉቦ፣ ውሸት፣ ስርቆት፣ ትዕቢት፣ ምቀኝነት፣.. ምሳሌ እንደጠቀስነው እንደ ሐሜቱ ናቸው፡፡ እነዚህና ሌሎችም "ለቁርባን አልገባም" እያልን እሽሩሩ የምንላቸው፣ የዲያብሎስ መንፈስ በምሽግነት የተደበቀባቸው፣ እንድላቀቃቸው በጽድቅ ቀናዒነት ያልጨከንባቸው፣ ከዘወትር ደቂቃዎቻችን መካከል ቦታ ያገኙ ኃጢአቶቻችን፥ የአዲስ ኪዳኑ ታላቅ መሥዋዕት ከሕይወታችን እንዲቋረጥ ለአጥፊው መንፈስ በብዙ አግዘዋል፡፡
2• ከኃጢአት ያለመላቀቅ ፍራቻ
ቅዱስ ቁርባንን የተመለከቱ እንደ ማኅበረሰብ ደንቦች ሲዛመቱ ከምንሰማቸው ወጎች መካከል "ቁርባን ዓለም በቃኝ ላለ ሰው ነው፣ ከተቆረበ በኋላ ኃጢአትን መሥራት ያልተላቀቀ ይቀሠፋል" የሚሉት ዝነኛ ሆነው ከጫፍ ጫፍ ተዳርሰዋል፡፡ ያሳዝናል!
ወገኖቼ፥ ክርስቶስ የሚያፈቅር እንጂ የሚቀሥፍ፣ የሚያከብር እንጂ የሚያዋርድ፣ የሚያነሳ እንጂ የሚጥል፣ የሚያቅፍ እንጂ የሚገፋ በጭራሽ አይደለም፤ ሆኖም አያውቅም፤ ወደፊትም አይሆንም፡፡ እንኳን ሰዎችን "ሥጋና ደሜን ከወሰዳችሁ በኋላ ኃጢአት ሠራችሁ" ብሎ ሊያጠፋ ይቅርና፥ የጠፉ ሰዎችን ሲያይ የሚያለቅስ የዋህ አባታችን እንደሆነ የሰቀለቺውን ኢየሩሳሌም ባየ ጊዜ እንባውን አፍስሶ ገርነቱን ገልጧል፡፡ "በቅዱስ ቁርባን ምክንያት" መቅሠፍት ይመጣል የሚሉ መነሻቸው ያልታወቁ ድምፆች፥ ዲያቢሎስ የነዛቸው ተንኮሎች እንደሆኑ ሕዝበ ክርስቲያኑ ሊገነዘብ ይገባዋል፡፡
አዎ፤ የጌታን ሥጋና ደም ሳይገባን (ገ ላልቶም ጠብቆም ይነበብ) መውሰድ አይፈቅድም (1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 11፥27)፡፡ ይሄ የሕግ ድንበር የተሰመረው ግን በመሢሑ በሥጋ መምጣት ያላመኑ፣ አምነውም በስሙ ያልተጠመቁ፣ የመስቀሉን ፍቅር ያልተቀበሉ፣ የቅዱስ ቁርባንን ሚሥጢር ያልተማሩ፣ መንፈሳዊ ኃይልን ለመፈታተን የሚቀበሉ፣ ለሌላ ድብቅ ተልዕኮና አጀንዳ የቀረቡ፣ ከመቁረብ በፊት ንስሐ ያልወሰዱ ሲኖሩ ለማረም ተፈልጎ እንጂ ክርስቲያኖችን ለማስፈራራት ታስቦ አይደለም፡፡ እንደውም ክርስቲያን ከክርስቶስ እንጀራና ጽዋ የማይካፈል ከሆነ ነው ዕዳ ያለበት፡፡
BY በማለዳ ንቁ ቁጥር ! ፪
Share with your friend now:
tgoop.com/bemaledanek/2752