tgoop.com/biryalew/834
Last Update:
የካቲት 12 ቀን የሰማዕታት ቀን
የካቲት ሚካኤል መቼ ተከበረ
ዶማ ይዞ ዋለ ሰው እየቆፈረ!!
<< ኢትዮጵያውያን ሁሉ በሰላምና በፍቅር ከቤተ መንግሥቱ ግቢ ተሰበሰቡ።ጥቂት ቆይቶ ግራዚያኒና መኳንንቱ ከተቀመጡበት ጠረጴዛ አጠገብ ቦምቦች ተወረወሩ። ቦምቡ እንደተጣለ ግራዚያኒ ጠረጴዛው ስር ተደበቀ።ሌሎች ኢጣሊያኖች ግን ከመሬት ተኙ። ቦምቡን የጣለው በኢጣሊያኖቹ ዘንድ በአስተርጓሚነት የሚሰራ የኤርትራ ክፍለ ሀገር ተወላጅ ነው።
<< ለጥቂት ጊዜ ፀጥ አለ።ኢጣሊያኖቹ ሌላ የሚወረወር ቦምብ እንደሌለ ካወቁ በኋላ ከተኙበት ተነሱ። ወዲያው ካርቴሲ ወደ ኢትዮጵያውያን መኳንንት ሽጉጡን አነጣጥሮ የመጀመሪያዋን አንድ ጥይት ተኮሰ። ካራቢኜሪዎችም ምሳሌውን ተከተሉ። በጥቂት ጊዜ ውስጥም በዚያ ግቢ 300 ሬሳዎች ተከመሩ።
<< ኃይለኛና ተገቢ ያልሆነ ጭፍጨፋ ነበር። ሽማግሌዎች፣ እውሮች፣ እግር የሌላቸው ለማኞች፣ ድሆች እናቶች ከነልጆቻቸው ነበሩበት። ባለጥቁር ሸሚዞች በግቢው እየተሯሯጡ በሕይወት ያለ ኢትዮጵያዊ ይፈልጉ ነበር።ከሬሳዎቹ መሀልም የሚተነፍስ እንዳለ እያሉ እየመረመሩ ይገድሉ ነበር። . . .<< ምን ዓይነት አጨካከን ነው? ደም እንደ ውሃ ሲፈስ በየመንገዱ ላይ ያየሁት የዚያን ጊዜ ነው። የወንዶች፣ የሴቶች፣ የልጆች ሬሣ በያለበት ተኝቷል።
ወዲያውም ከባድ የቃጠሎ ጭስ ተነስቶ ከተማዋን አጨለማት። የሕዝቡ ቤት ከተፈተሸ በኋላ ሰዎቹ በውስጡ እንዳሉ ቤቱ በእሳት ይቃጠላል። ቃጠሎው ቶሎ እንዲያያዝም በቤንዚንና በዘይት ይጠቀሙ ነበር። ሰዉ እሳቱን እየሸሸ ከቤቱ ሲወጣ በመትረየስ ይገድሉታል። ሌሊቱንም ሲገድሉና ሲያቃጥሉ አደሩ። . . .
<< መኪናዎች እየዞሩ ሬሣ ያነሳሉ። ባለጥቁር ሸሚዞች ወደ ኢጣሊያ ባንክ እየገቡ ሌሊት የሰረቁትን ብርና ወርቅ ያስቀምጣሉ። ዘረፋው በቤት ውስጥ ብቻ አልነበረም። ከሚገድሏቸው ሴቶች አንገትና ጆሮ ላይ የሚገኘውን ወርቅ ሁሉ ይወስዱ ነበር። << ሕክምና በምሰራበት ቦታ ብዙ ኢጣሊያኖች ይመጡ ነበር።
እያንዳንዱ ኢጣሊያም ምን ያህል ሰው እንደገደለ በኩራት ይናገራል። አንዳንዶቹ 80 ገደልኩ ሲሉ አንዳንዶቹ ደግሞ መቶ እንደገደሉ በኩራት ይናገራሉ። አንድ ኢጣሊያዊ ብቻ እያዘነ "እኔስ የገደልኩት ሁለት ብቻ ነው" ብሎ ሲናገር ሰምቻለሁ። ... የማልረሳው ነገር ግድያው እንዲቆም በተደረገበት ጊዜ "ታላቁ ግራዚያኒ ለሕዝብ በማዘን ግድያው ይቁም ብለዋል" ተብሎ የተነገረው ነው። ግሩም አዘኔታ፥ ...>>. . . . .
(ይህ በወቅቱ አዲስ አበባ የነበረው ሀንጋሪያዊ ሐኪም ዶክተር ላዲስላስ ሳቫ የዓይን ምስክርነት ነው።) የካቲት 12 ቀን በተጀመረው እልቂት በሶስት ቀን ውስጥ 30,000 ሰዎች በአዲስ አበባ ከተማ ብቻ ከተገደሉ በኋላ ሌላው እየታፈሰ ወደ በረሃ እሥር ቤቶች ተላከ።
የኢትዮጵያና የጣሊያን ጦርነት( ጳውሎስ ኞኞ)
@biryalew
@biryalew
BY ✍✍✍ብዕር ያለው ያውጋ/bir yalew yawga✍✍✍
Share with your friend now:
tgoop.com/biryalew/834