tgoop.com/ethyas/1268
Last Update:
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን። የልዑል እግዚአብሔር ቤተሰቦች እንደምን ቆያችሁ! የዛሬ እናስተዋውቃችሁ መርሀግብር እነሆ በሁለት ክፍሎች አቀረብንላችሁ።
መግቢያ ጠባቂዋ ሥዕለ ማርያም
መግቢያ ጠባቂዋ በመባል የምትታወቀውና ቅዱስ ሉቃስ ሣላቸው ከሚባሉ ቅዱሳት የእመቤታችን ሥዕላት መካከል ስትሆን በምስራቁ የባይዛነቲን ክርስቲያን ሀገር በየካቲት 4 በዓሏ የሚታሰብላት የእመቤታችን ሥዕል ናት፡፡ የዚህች ሥዕል መለያዋ ደግሞ ከቀኝ ጒንጯ ደም በማፍሰስ የፈጸመችው ታላቅ ተአምር ነው፡፡ ይህች ሥዕል በአሁኑ ሰዓት በአቶስ ተራራ ላይ በሚገኘው ገዳም የምትገኝ ሲሆን ከቀድሞው ሥዕል የፊት ገጹ ብቻ በሚታይ መልኩ ከሌላው የሥዕሉ
ክፍል በወርቅና በብር የተለበጥ ነው፡፡
የዚህችን ሥዕል ታሪክ እነሆ፡፡
ይህች ሥዕል በትውፊት ቅዱስ ሉቃስ ሣላቸው ከሚባሉት ሥዕል አንዷ ስትሆን በዘጠነኛው መ.ክ.ዘ. ላይ ኒቅያ (ታናሽ እስያ) በአንድ ባልቴት ቤት ውስጥ ነበረች፡፡ በዚያን ወቅት ከ829-842 ዓ.ም. በቤዛንታይን የነገሠው ንጉሥ ቴዎፍሎስ በቅዱሳት ሥዕላት ላይ
በክፋት ተነሳሥቶ ዐዋጅ በማወጁ ወታደሮቹ በርሱ ትእዛዝ በእያንዳንዱ ቤት እየዞሩ ቅዱሳት ሥዕላትን ለማጥፋት ፍተሻ ያደርጉ ነበር፡፡ ይህች ሴትም በሥዕሏ ፊት መብራትን እያበራች ከልጇ
እንድታማልዳት ትማፀን ነበር፡፡ የከሓዲው ንጉሥ ወታደሮቹም የአምላክ እናት ሥዕል በቤቷ እንዳለች በማወቃቸው ወደ ቤቷ በድንገት ዘልቀው ገቡ፤
ከመካላቸውም አንዱ ወታደር የእመቤታችንን ሥዕሏን በያዘው ጦር ጒንጯ ላይ ወጋት፡፡ ኾኖም ግን በእግዚአብሔር ድንቅ ሥራ ይኽ ክፉ ሥራው በተአምር
ተተክቶ፤ ከተወጋው ከአምላክ እናት ፊት ላይ ደም ይፈስስ ጀመር፡፡ ይኽን ግሩምና ድንቅ ተአምር ባዩ ጊዜ ወታደሮቹ
ደንግጠው ሲሸሹ የእመቤታችን ሥዕልን የወጋው ወታደር ግን በተፈጸመው ድንቅ ተአምር የቅዱሳት ሥዕላት መጥፋት አለባቸው ከሚለው ክህደት ተጸጽቶ ንስሐ ገብቶ ወደ ገዳም ገባ፡፡ ለባልቲቱም ሥዕሉን ሸፍና እንድትደብቀው ሌላ ተጨማሪ ጉዳት እንዳይደርስበት ወታደሩ መከራት፡፡ ሴቲቱም ይኽነን ድንቅ ተአምር ባየች ጊዜ ሌሊቱን ሙሉ በሥዕሏ ፊት መብራትን አብርታ በአምላክ እናት በቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕል ፊት ስትጸልይ ዐደረች፡፡ በነጋታውም በእግዚአብሔር ፈቃድ ከጒንጮቿ ደም የፈሰሳትን የአምላክ እናት ሥዕሏን በባሕሩ ላይ እንድታስቀምጥ ታዘዘችና አስቀመጠቻት፤ሥዕሏም በባሕሩ ላይ ቀጥ ብላ በመቆም እና
በመንሳፈፍ ሳትሰምጥና ሳትረጥብ በማዕበሉ እየተነዳች ወደ ምዕራብ አቅጣጫ ጉዞዋን አድርጋ ወደ
አቶስ ተራራ ደረሰች፡፡
የባልቴቱ ልጅም ችግሩን በመሸሽ በኋላ ዘመን በአቶስ ገዳም መንኮሰ፡፡ በገደሙ ሳለም ደም ስላፈሰሰችው ሥዕል እና እናቱ በባህር ላይ ባስቀመጠቻት ወቅት
ሳትሰምጥ ቀጥ ብላ መንሳፈፏን ይናገር ነበር፡፡ ይህ የነገራቸው ተአምር ደግሞ በገዳሙ ሲኖሩ በነበሩ አባቶች ሲወርድ ሲዋረድ ቀጠለ፡፡ ከብዙ ዓመታት በኋላ (1004 ዓ.ም. አካባቢ) ከዕለታት
በአንዳቸው ምሽት በአቶስ ተራራ የአይቬሮን(Iviron monastery) ገዳም መነኮሳት የብርሃን ምሰሶ በባሕሩ ላይ ተተክሎ እንደ ፀሓይ ሲያበራ ተመለከቱ፡፡
ይኽም ተአምር ለተካታታይ ቀናቶች በመቀጠላቸው በዚያ የተቀደሰ ተራራ በምናኔ ያሉ አባቶች ኹሉ በአንድ ላይ ተሰባስበው በማድነቅ የብርሃን ምሰሶ ወደተተከለበት የአምላክ እናት ሥዕል በላዩ ላይ ወደ ተንሳፈፈበት ወደ ባሕሩ በመውረድ ወደ ሥዕሏ ለመጠጋት ቢሞክሩም ሥዕሏ ወደ ኋላዋ እየተመለሰች ሊያነሷት አልተቻላቸውም፡፡ በዚያው የአይቮሪዮን ገዳም ረድእ (የጉልበት አገልጋይ) ኾኖ የሚኖር አባ ገብርኤል የተባለው መነኩሴ ብቻ ሥዕሏን ከባሕር ውስጥ ማንሣት የሚችል እንደኾነ የአምላክ እናት ለመነኮሳቱ ገለጠችላቸው፤ በተመሳሳይም ለአባ ገብርኤል እመቤታችን ተገልጣለት“ወደ ባሕሩ ኺድ፤ ማዕበሉንም ሳትፈራ በባሕሩ ውስጥ በእምነት ተጓዝ፤ እናም ኹሉም ለዚኽ አንተ ላለኽበት
ገዳም ያለችን ፍቅርና ርኅራኄ ምስክር እንዲኾኑ፤ ሥዕሌን ከባሕር አውጣ” በማለት ነገረችው፡፡
ይቀጥላል........
BY ኢትዮጵያ የስላሴ የክብራቸው መገለጫና መመስገኛ ምድር
Share with your friend now:
tgoop.com/ethyas/1268