tgoop.com/menefesawinet/9818
Last Update:
🕊
[ ✞ እንኩዋን ለሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ✞ ]
🕊 † ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያ † 🕊
ከ ፲፪ [12] ቱ ቅዱሳን ሐዋርያት አንዱ የሆነው ቅዱስ ቶማስ ብዙ መከራን በማሳለፉና የጌታችንን ጐን በመዳሰሱ ይታወቃል::
ቅዱስ ቶማስ እንደ ሌሎቹ ሐዋርያት በእሥራኤል ተወልዶ በዚያውም በሥርዓተ ኦሪት አድጐ ገና በወጣትነቱ የሰዱቃውያንን ማሕበር ተቀላቅሏል:: ሰዱቃውያን ሰው ከሞተ በሁዋላ አይነሳም [አልቦ ትንሳኤ ሙታን] የሚሉ ናቸው::
መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ማስተማር ሲጀምር ግን ቅዱስ ቶማስ ከነበረበት ማሕበር ወጥቶ ጌታችንን ተከተለ:: ጌታችንም ከ ፲፪ [12] ቱ ሐዋርያት አንዱ ይሆን ዘንድ ሾመው:: የቀደመ ስሙ ዲዲሞስ ሲሆን ጌታችን ቶማስ ብሎታል::
ቅዱስ ቶማስ ጌታ አልዓዛርን ለማስነሳት በሔደ ጊዜ ሌሎች ሐዋርያት ጌታን "አይሁድ ይገድሉሃል ቅር" ሲሉት እርሱ ግን "እንሒድና አብረን እንሙት" ሲል ፍቅሩን አሳይቷል:: [ዮሐ.፲፩፥፲፮] (11:16)
ጌታችን ትንሳኤውን ለደቀ መዛሙርቱ በገለጠ ጊዜ ያልነበረው ቶማስ ካላየሁ አላምንም አለ:: ምክንያቱም :-
፩. ለጌታችን ከነበረው ፍቅር የተነሳ እውነት አልመስልህ ቢለው
፪. አንድም ሌሎቹ ሐዋርያት ትንሳኤውን አየን እያሉ ሲያስተምሩ እኔ ግን ሰማሁ ብየ ማስተማሬ ነው ብሎ በማሰቡ ነበር::
ለጊዜው ጌታ ተገልጾ ቢገስጸው "እግዚእየ ወአምላኪየ [ጌታየና አምላኬ]" ብሎ ፍጹም ሃይማኖቱን ገልጿል:: ለፍጻሜው ግን የጌታችንን ጎን [መለኮትን] ይዳስስ ዘንድ ባለቤቱ እንዳደለው ያጠይቃል:: መለኮትን የዳሰሰች ይሕቺ ቅድስት እጁ ዛሬም ድረስ ሕያው ናት:: በሕንድ ቤተ ክርስቲያን ውስጥም በክብር ተቀምጣለች::
ቅዱሳን ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ተቀብለው ሐገረ ስብከት ሲከፋፈሉ ለቅዱስ ቶማስ ሕንድና በዙሪያዋ ያሉ ሃገራት ደረሱት:: ከዚህ በሁዋላ ነው እንግዲህ ዘርዝረን የማንጨርሰውን ተጋድሎ የፈጸመው:: ቅዱሱ በነበረው ፍጹም ትጋት አባቶቻችን "ዘአሠርገዋ ለብሔረ ሕንደኬ [ሕንድን በወንጌል ያስጌጣት]" ሲሉ ያከብሩታል::
ቅዱስ ቶማስ ንጉሥ ሉክዮስንና የሃገሩን ሕዝብ ለማሳመን በችንካር መሬት ላይ ወጥረው ቆዳውን ገፈውታል:: ቆዳውንም እንደ ገና ሰፍተው: አሸዋ ሞልተው አሸክመውታል::
በየመንገዱ የተገፈፈ ገላውን ጨው ቢቀቡት በጎች መጥተው ግጠው በልተውታል:: በዚሕ ምክንያት :-
"ኩሉ የአኪ እንዘ የአኪ ዘመኑ:
አባግዒሁ ለቶማስ እስመ አራዊተ ኮኑ" ብለዋል ሊቃውንቱ::
በሁዋላ ግን ከፎቅ ወድቃ የሞተችውን የንጉሡን ሚስት በተገፈፈ ቆዳው በማዳኑ ሁሉም አምነው ተጠምቀዋል::
ቅዱሱ ሐዋርያ ልክ እንደ ቅዱስ ዻውሎስ አንዳንዴ በፈሊጥ: ሌላ ጊዜም በመከራ ለወንጌልና ለቤተ ክርስቲያን ተጋድሏል:: ያለ ማቁዋረጥም ከሕንድ እስከ ሃገራችን ኢትዮዽያ ድረስ ለ፴፰ [38] ዓመታት ወንጌልን ሰብኩዋል::
በመጨረሻም በ፸፪ [72] ዓ/ም በዚሕች ቀን በሰማዕትነት አርፏል:: መቃብሩና ቅድስት እጁ ዛሬ ድረስ ሕንድ ውስጥ አሉ:: ከኘሮቴስታንቶች በቀር መላው ዓለም ያከብረዋል::
እንደ አባቶቻችን ትርጉም ቶማስ [ቶማስስ] ማለት ጸሐይ [ኦርያሬስ] እንደ ማለት ነው:: በተሰጠው የወንጌል ጸጋ በሃገረ ስብከቱ አብርቷልና::
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከአገልጋዩ ቅዱስ ቶማስ ጸጋ በረከት ይክፈለን::
🕊
[ † ግንቦት ፳፮ [ 26 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት ]
፩. ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያ [ከ ፲፪ [12]ቱ ሐዋርያት]
፪. ቅድስት አርሶንያ [የቅዱስ ቶማስ ተከታይ]
፫. አቡነ ሐብተ ማርያም ጻድቅ
[ † ወርሐዊ በዓላት ]
፩. አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ዘሐይቅ
፪. ቅዱሳን ሰማዕታተ ናግራን
፫. አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን
" ደጆች ተዘግተው ሳሉ ኢየሱስ መጣ:: በመካከላቸውም ቆሞ "ሰላም ለእናንተ ይሁን" አላቸው:: ከዚያም በሁዋላ ቶማስን "ጣትህን ወደዚህ አምጣና እጆቼን እይ:: እጅህንም አምጣና በጐኔ አግባው:: ያመንህ እንጂ ያላመንህ አትሁን" አለው:: ቶማስም "ጌታዬ አምላኬም" ብሎ መለሰለት:: ኢየሱስም "ስላየኸኝ አምነሃል:: ሳያዩ የሚያምኑ ብጹዓን ናቸው" አለው:: " [ዮሐ.፳፥፳፮-፳፱] (20:26-29)
† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †
ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ
https://www.tgoop.com/menefesawinet
BY መንፈሳዊ ትምህርት ዘኦርቶዶክስ
Share with your friend now:
tgoop.com/menefesawinet/9818