tgoop.com/menefesawinet/9824
Last Update:
🕊
† በስመ አብ : ወወልድ : ወመንፈስ ቅዱስ : አሐዱ አምላክ . . . አሜን :: †
🕊 † አቡነ ሃብተ ማርያም ጻድቅ † 🕊
እኒህ ጻድቅ የሃገራችን ኮከበ ገዳም ናቸው:: "ጽድቅና ትሩፋት እንደ ሃብተ ማርያም" እንዲሉ አበው:: ባሕር ከሆነ ጣዕመ ሕይወታቸው ጥቂቱን ለበረከት እንካፈል::
ጻድቁ መካነ ሙላዳቸው ሽዋ [የራውዕይ] ውስጥ ሲሆን አባታቸው ፍሬ ቡሩክ : እናታቸው ደግሞ ቅድስት ዮስቴና ትባላለች:: በተለይ ቅድስት ዮስቴና እጅግ ደመ ግቡ : ምጽዋትን ወዳጅ : ቡርክት ሴት ነበረች:: እንዲያውም ከጻድቁ መወለድ በፊት መንና ጭው ካለ በርሃ ገብታ ነበር::
ግን የበቃ ግኁስ አግኝቷት "ከማሕጸንሽ ደግ የሥላሴ ባርያ አለና ተመለሽ" ብሏት እንደ ገና ተመልሳለች:: ጻድቁን ወልዳ አሳድጋም እንደ ገና መንና በተጋድሎ ኑራ 7 አክሊላትን ተቀብላ ዐርፋለች::
ወደ ጻድቁ ዜና ሕይወት ስንመለስ አቡነ ሃብተ ማርያም ገና ሕጻን እያሉ ከእናታቸው ጋር ቆመው ሲያስቀድሱ "እግዚኦ መሐረነ ክርስቶስ" ሲባል ይሰማሉ:: ይሕችን ጸሎት በሕጻን አንደበታቸው ይዘው ሌሊት ሌሊት እየተነሱ "ማረን እባክህን?" እያሉ ይሰግዱ ነበር::
የ ፭ [5] ዓመት ሕጻን እንዲህ ሲያደርግ ማየቱ በእውነት ይደንቃል:: ትንሽ ከፍ ብለው በእረኝነት ሳሉም ፍጹም ተሐራሚና ጸዋሚ ነበሩ:: ጸጋው ስለ በዛላቸውም ልጅ ሆነው ብዙ ተአምራትን ሰርተዋል:: የፈጣሪውን ስም ያቃለውን አንድ እረኛም በዓየር ላይ ሰቅለው አውለውታል::
ከዚያ ግን ለአካለ መጠን ሲደርሱ ወደ ት/ቤት ገብተው : መጻሕፍትንም አጥንተው መንነዋል:: በአባ መልከ ጼዴቅ እጅ ከመነኮሱ በሁዋላ የሠሩትን ትሩፋትና የነበራቸውን ተጋድሎ ግን የኔ ብጤ ደካማ ሰው ሊዘረዝረው አይችልም::
- ባሕር ውስጥ ሰጥመው ፭፻ [500] ጊዜ ይሰግዳሉ::
- በየቀኑ ፬ [4] ቱን ወንጌልና ፻፶ [150] መዝሙረ ዳዊትን ይጸልያሉ:: (µ[መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ ታላቅ ጸሎት ነው]
- በ ፵ [40] ቀናት : ቀጥሎም በ ፹ [80] ቀን አንዴ ብቻ ይመገባሉ::
- ምግባቸው ደግሞ ሣርና ቅጠል ብቻ ነው::
- በየዕለቱ ያለ ማስታጐል ማዕጠንት ያሳርጋሉ:: [ካህን ናቸውና]
- ዘወትር በንጽሕና ቅዱስ ሥጋውን ይበላሉ : ክቡር ደሙን ይጠጣሉ::
- በፍጹም በልባቸው ውስጥ ቂምን : መከፋትን አላሳደሩም::
በእነዚህና በሌሎች ትሩፋቶቻቸው ደስ የተሰኘ ጌታም ለጻድቁ የእሳትና የብርሃን ሠረገላን ሰጥቷቸው በዚያ እየበረሩ ኢየሩሳሌም ይሔዱ ነበር:: ከብዙ የተጋድሎ ዘመናት በሁዋላም የክብር ባለቤት መድኃኒታችን ክርስቶስ አዕላፍ መላእክትን አስከተትሎ መጥቶ አላቸው::
፩. " ስለ እኔ ረሃብና ጥምን ስለ ታገስክ:
፪. ስለ ምናኔሕ:
፫. ስለ ተባረከ ምንኩስናህ:
፬. ስለ ንጹሕ ድንግልናህ:
፭. ቂምና በቀልን ስላለመያዝህ:
፮. ስለ ንጹሕ ክህነትህና ማዕጠንትህ:
፯. ቅዱስ ወንጌልን በፍቅር ስለ ማንበብህ ፯ [7] አክሊላትን እሰጥሃለሁ::"
"በሰማይም ከመጥምቁ ዮሐንስ ጐን : ፭፻ [500] የእንቁ ምሰሶዎች ያሉበትን አዳራሽ ሰጥቼሃለሁ:: በስምህ የሚለምኑ : በቃል ኪዳንህ የሚማጸኑትንም ሁሉ እንድምርልህ 'አማንየ! በርእስየ!' ብዬሃለሁ" አላቸው::
ቅዱሳን መላእክትም "ሃብተ ማርያም ወንድማችን" ሲሉ አቀፏቸው:: ጌታ ግን በዚያች ሰዓት አንድም ሦስትም ሆኖ ታያቸውና አቅፎ 3 ጊዜ ሳማቸው:: ከፍቅሩ ጽናትም የተነሳ ነፍሳቸው ከሥጋቸው ተለየች:: በዝማሬም ወሰዷት:: {ይህች ቀን [ግንቦት ፳፮ [26] ] ለጻድቁ ዕለተ ልደታቸው ናት::}
አምላከ አበው ወሰማዕት ጣዕመ ፍቅራቸውን: ክብራቸውን: ጸጋ በረከታቸውንም ይክፈለን::
🕊
"እግዚአብሔር ፍርድን ይወድዳልና:: ቅዱሳኑንም አይጥላቸውምና:: ለዘለዓለምም ይጠብቃቸዋል . . . ጻድቃን ምድርን ይወርሳሉ:: በእርስዋም ለዘላለም ይኖራሉ:: የጻድቅ አፍ ጥበብን ያስተምራል:: አንደበቱም ፍርድን ይናገራል:: የአምላኩ ሕግ በልቡ ውስጥ ነው:: በእርምጃውም አይሰናከልም::" [መዝ.፴፮፥፳፮-፴፩] (36:28-31)
† ወስብሐት ለእግዚአብሔር። †
ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ
https://www.tgoop.com/menefesawinet
BY መንፈሳዊ ትምህርት ዘኦርቶዶክስ
Share with your friend now:
tgoop.com/menefesawinet/9824