tgoop.com/ortodoxtewadochannal/4200
Last Update:
በእንተ ቅዱስ መስቀል (#በቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ)
የጌታችን የክርስቶስ መስቀል ለእንደ ምን ያለ ታላቅ በረከት ምክንያት እንደ ኾነልን እናስበው፡፡ ምንም እንኳን ከአፍአ ሲታይ የጌታችን መስቀል አሳዛኝና አሰቃቂ ቢመስልም፥ እንደ እውነቱ ግን ደስታንና ሐሴትን የተሞላ ነው፡፡ መስቀል የቤተ ክርስቲያን መድኃኒት ነውና፤ መስቀል ተስፋ ለሚያደርጉት መመኪያቸው ነውና፤ መስቀል ጠላቶች [ደቂቀ አዳም] ከእግዚአብሔር ጋር የሚታረቁበት [የታረቁበት]፥ ኃጥአንም ወደ ክርስቶስ የተመለሱበት [አሁንም የሚመለሱበት] ነውና፡፡
በመስቀል ከጠላትነት ድነናል፤ በመስቀል ወደ እግዚአብሔር አንድነት ተመልሰናል፡፡ በመስቀል ከግብርናተ ዲያብሎስ አርነት ወጥተናል፤ በመስቀል ከሞትና ከጥፋት ድነናል፡፡ ብሥራተ መስቀል ባልተነገረበት ዘመን በሞት ጥላ ሥር ተይዘን ነበር፤ አሁን ብሥራተ መስቀል በተገለጠበት ጊዜ ግን ህልውና እንኳን እንደሌለው አድርገን ቈጥረን የዘለዓለም ሕይወትን እየናፈቅን ሞትን ንቀነዋል፡፡ ብሥራተ መስቀል ባልተነገረበት ዘመን ለገነት እንግዶች ነበርን፤ መስቀል በተገለጠ ጊዜ ግን ወንበዴስ እንኳን ለገነት የተገባ ኾኖ ተገኘ፡፡ የሰው ልጅ እንደዚህ ካለ ጨለማ መጠን ወደ ሌለው ብርሃን፣ ከሞት ወደ ዘለዓለማዊ ሕይወት፣ ከመዋቲነት ወደ ኢመዋቲነት ታድሶ ተሸጋገረ፡፡ ዓይነ ልቡና ባለማወቅ ጽልመት ከመታወር ድኖ በመስቀል የዕውቀት ብርሃን ተጥለቀለቀ፡፡ እዝነ ልቡና ካለማመን ድንቁርና ወጥቶ የእግዚአብሔርን ቃል ወደ መስማት ተመለሰ፤ ዕውራንም [መንፈሳዊ] ብርሃናቸው ተመልሶላቸው የእግዚአብሔርን ክብር ማየት ተችሎአቸዋል፡፡ በቅዱስ መስቀሉ የተሰጡን ሀብታት እነዚህ ናቸው፡፡ በቅዱስ መስቀሉ ያልተሰጡን በረከቶችስ ምን አሉ?
እነሆ ቅዱስ መስቀሉ ተገልጧል፤ በእግዚአብሔር ማመንም ተመልሷል፤ እውነትም [ወንጌልም] ወደ ዓለም ኹሉ ደርሷል፡፡ ቅዱስ መስቀሉ ተገልጧል፤ ሰማዕታትም [ከመስቀል በኋላ ሞት ሞት መኾኑ እንደ ቀረና የሹመት የሽልማት ማሳ መኾኑን ዐውቀው አብረው] ተገልጠዋል፤ በክርስቶስ ማመንም በኹሉም ዘንድ ተሰራጭቷል፡፡ ቅዱስ መስቀሉ ተገልጧል፤ [በእርሱም ሞት ራሱ ሞቷልና] ትንሣኤ ሙታንም ተገልጧል፤ ሕይወትም ታይታለች፤ መንግሥተ እግዚአብሔርም እንደዚሁ እርግጥ ኾናለች፡፡ ቅዱስ መስቀሉ ለእነዚህ ኹሉ ነገሮች ምክንያት ኾኗል፡፡ በመስቀሉ እግዚአብሔርን ማመስገን ተማርን፡፡ እንግዲህ ከቅዱስ መስቀሉ ይልቅ ሌላ የተወደደ ምን አለ? እኮ ከቅዱስ መስቀሉ በላይ ለነፍሳችን የሚረባት [የረባት፣ የጠቀማት] ሌላ ምን አለ? ስለዚህ በሙሉ ልባችን ይህን እንመስክር እንጂ ስለ ቅዱስ መስቀሉ ለመናገር ቅንጣት ታህልስ እንኳን አንፈር፡፡
ክርስቶስ በቅዱስ መስቀል ላይ ተሰቀለ፤ ዲያብሎስም በድን ኾነ፡፡ ክርስቶስ በቅዱስ መስቀል ላይ እጆቹን ዘረጋ፤ ለዓለምም የመዳን መንገድ ተሰጠ፡፡ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ተቸነከረ፤ ነፍሳትም ኹሉ ከእስራታቸው ተፈቱ፡፡ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ዋለ፤ ፍጥረታትም ኹሉ ከጥፋት ባርነት ነፃ ወጡ፡፡ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ነፍሱን አሳልፎ ሰጠ፤ እንግዳ ነገርም ለዓለም ኹሉ ታየ ፀሐይ ብርሃኗን ከለከለች ንዑድ ክቡር የሚኾን ነቢዩ አሰምቶ እንደ ተናገረው - እንዲህ ሲል፡- “በዚያን ቀን ፀሐይ በቀትር ይገባል፤ ብርሃንም በምድር ላይ በቀን ይጨልማል” (አሞ.8፡9)፡፡ ተወዳጆች ሆይ! የነቢዩ ቃል እንደ ምን ያለ ግሩም ምሥጢር በውስጡ ቋጥሮ እንደ ያዘ ታያላችሁን? እዚህ ላይ የኹላቸውም -የእስራኤላውያንም የአሕዛብም - ግብር ተገልጧል፤ ኹላቸውም በአንድነት በድለዋልና፡፡
እንደ ኦሪቱ ሕግ በዓላትን የሚያከብሩት ያዝናሉ፤ በመዝሙር ፈንታም በኢየሩሳሌም ላይ.ያለቅሳሉ፡፡ ከእንግዲህ ወዲህ ኢየሩሳሌም የተቀደሱትን ሥርዓተ አምልኮዎችን ይዛ አትቀጥልምና፤ ከእንግዲህ ወዲህም በእርሷ ዘንድ በዓላት አይከበሩምና፡፡ የአሕዛብ አገራትም እንደዚሁ ኃጢአታቸውን እየተናዘዙ ያዝናሉ፤ መጽሐፍ “የሚያዝኑ ብፁዓን ናቸው” እንዳለ ኀዘን የበረከት ምንጭ ነውና ይተክዛሉ (ማቴ.5፡4)፡፡ አዎ! ትርጉም ለሌላቸው በዓላቶቻቸውና ሥርዓት ለሌላቸው ዘፈኖቻቸው ለርኵሳት መናፍስት ይቀርብ እንደ ነበረ ዐውቀው ያዝናሉ፤ ይተክዛሉም፡፡ ዛሬ አሕዛብ ያከናውኑአቸው ለነበሩት ክፉ ክፉ ነገሮች እንዴት እንደሚጸጸቱባቸው አስተውሉ፤ ከነቢዩ ጋር በአንድነት እንዲህ ይላሉና፡- “በድለናል፤ በሐፍረታችንም ጠፍተናል፤ በዓመፃ ተሞልተናልና ኃጢአታችን ሸፍናናለች፡፡ እንደ አባቶቻችን በድለናል፡፡”
እንግዲያውስ እኛም ስለ ሠራናቸው ኃጣውእ እናልቅስ፤ እንዘንም፡፡ ተስፋችንን በእርሱ ላይ.አኑረን ወደ ቅዱስ መስቀሉ እንጠጋ፡፡ እኛ ሥራ ሠርተን አንበቃምና ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ክብሩና ጌትነቱ አንድ በሚኾን በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ቸርነትና ሰውን መውደድ የመንግሥቱ ወራሾች እንኾን ዘንድ በመስቀሉ [ቃል] ተምረን አሳባችንን በሰማያት እናኑር፤ ይእዜኒ ወዘልፈኒ ለዓለም ወለዓለም፥ አሜን!!!
ለኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ልጆች👇
•➢ ሼር // SHARE
@ortodoxtewadochannal
@ortodoxtewadochannal
BY ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ መንፈሳዊ አገልግሎት
Share with your friend now:
tgoop.com/ortodoxtewadochannal/4200