tgoop.com/sratebetkrstyane/6934
Last Update:
፩ኛ. የጾሙ የመጀመሪያ ሳምንት ከቅዳሜ ኅዳር ፲፭ እስከ ኅዳር ፳፩ ቀን ፳፻፲ወ፮ ዓ/ም በሁሉም የሀገራችን ክፍልና ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ባለችበት በመላው ዓለም የንሥሓ፣ የጾም፣ የጸሎትና የምኅላ ሳምንት እንዲሆን፤
፪ኛ. በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ በአድባራት አስተዳዳሪዎች፣ በአጥቢያ አለቆችና በገዳም አበምኔቶች መሪነት ሁሉም ዲያቆናት፣ ቀሳውስት፣ መነኰሳት፣ ሰባክያንና ሊቃውንት በሙሉ በየመዐርጋቸው ልብሰ ተክህኖና ወጣት የሰንበት ትምህርት ቤት ዩኒፎርማቸው ለብሰው፣ ሁሉም ምእመናን ጋር በአንድነት በዐውደ ምህረት ጸሎተ ምኅላውን እንዲያደርሱ፤
፫ኛ. በላው ሕዝበ ክርስቲያን ከሊቅ እስከ ደቂቅ፣ ሕፃናት፣ ወጣቶች፣ እናቶች አባቶች አረጋውያን ሁሉ የቻለ በቤተ ክርስቲያን፣ ያልቻለ በያለበት ሆኖ የተጣላ ታርቆ፣ በፍቅርና በአንድነት፣ በእውነተኛ ንሥሓና ጸጸት በምኅላው እንዲሳተፍ፤ በማእከል የሚደረገው ጸሎተ ምኅላ በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ መሪነት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት በተገኙበት በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያም ገዳም ሆኖ በመገናኛ ብዙኀን የቀጥታ ሥርጭት ለመላው ዓለም እንዲተላለፍ፤
፬ኛ. በመጀመሪያው የሱባኤ ቀን ኅዳር ፲፭ ቀንና፣ በሰባተኛው ቀን ኅዳር ፳፩ ቀን በጸሎተ ምኅላው በሚደረግበት ጊዜ ታቦቱ ከመንበሩ ተነሥቶ በዐውደ ምኅረት በቀሳውስት እንዲከብር ሆኖ፤ በሁሉም የምኅላው ቀናት ሥዕለ ማርያም፣ ወንጌልና መስቀል ወጥቶ በአራቱ መዐዝን ሥርዓተ ጸሎተ ምኅላው ከጸሎተ ወንጌል ጋር በየቀኑ በነግህና በሠርክ የሥራ ሰዓትን በማይነካ ሁኔታ እንዲፈጸም፤
፭ኛ. በየዕለቱ የሚነበቡት የወንጌል ክፍሎችን ስለ ሰላም፣ ስለንሥሓና ጸጸት፣ ስለ ፍቅርና አንድነት፣ ስለ በጎነትና መደማመጥ፣ ስለመሰማማትና ጥላቻን ስለማራቅ እንዲሆን፤
፮ኛ. በሰፊህና በአንቀዓድዎ፣ በሰጊድና በአስተብርኮ፣ ምኅላው ከደረሰና፣ ጸሎተ ወንጌል ደርሶ ዕለቱ ወንጌል ከተነበበ በኋላ በአንድነት የንሥሓ መዝሙር በመዘመር፣ ሕዝበ ክርስቲያን ስለሀገራቸውና ስለሰው ልጆ ደኅንነት እያሰቡ ወደቤታቸው እንዲሄዱ፤
፯ኛ. ከመጀመሪው ሳምንት በኋላ እስከ በዓለ ልደት ድረስ የሰርክ ምህላ ሳይቋረጥ መደበኛው ሥርዓተ ጾምና ጸሎት እንዲቀጥል፣ የቤተ ክርስቲያንን ታላቅነት፣ የአበውን ተቀባይነት በሚገለጽ፣ በቀጣይም ሁሉም ኦርቶዶክሳውያን በመንፈሳዊ ጽናት የሰላም ልዑካን ሆነው እንዲቀጥሉ በሚያደርግ ሁኔታ እንዲፈጸም፤
፰ኛ. አስቀድሞ የደረሰውንና፣ እየደረሰብን ያለው ችግር የጦርነትና የግጭት ብቻ ሳይሆን የረሀብ፣ የድርቅ፣ የኑሮ ውድነት፣ የመፈናቀልና የስደት ጭምር ስለሆነ ከጸሎትና ምኅላችን ጎን ለጎን መረዳዳትና መተዛዘን፣ ርኅራሄና መደጋገፍ አብሮ እንዲፈጸም፤
፱ኛ. ይኽንኑ መልእክት መላው ዓለም እንዲውቀው፣ በተለይም የኦሬንታል ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት በጸሎት እንዲያስቡን፣ የጸሎታችንና የምኅላችን መነሻ ምክንያቱ የሀገራችን ወቅታዊ ችግር ቢሆንም የምንጸልየው ለመላው ዓለም መሆኑ ተገልጾ በደብዳቤ እንዲላክ እንዲደረግ፣ በማለት ቅዱስ ሲኖዶስ ጥብቅ መመሪያ አስተላልፏል፡፡
እግዚአብሔር አምላካችን በእንባና በንሥሓ የምናቀርበውን ጸሎተ ምኅላችንን በምህረቱ ተቀብሎ ሀገራችንን ሰላም ያድርግልን፣ ሕዝባችንን ይጠብቅልን፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
የኢትዮጵያ ኦርቶዶከስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን
ቅዱስ ሲኖዶስ
BY ✝️ስርዓተ ቤተክርስቲያን መመሪያ ✝️
Share with your friend now:
tgoop.com/sratebetkrstyane/6934