Telegram Web
የትግራዩ ጦርነቱ ጉዳት ቁጥራዊ መረጃዎች
(ተስፋኣብ ተሾመ)
* * *

የትግራዩ ጦርነት ቁስል ሳያገግም ወደ ሌላ ጦርነት ገብተናል። ከቀደመው ሳንማር አዲስ ስህተት ውስጥ ተዘፍቀናል።
ከጦርነቱ ምን አጠኘን? ምንም! ከጦርነቱ ምን ተማርን? ምንም!
በጦርነቱ ያጣነው ብዙ ነው። ምናልባት ቁጥራዊ መረጃዎች ቆም ብለን እንናስብ ይረዱን ከሆነ የውድመቱን መጠን በቁጥር አስደግፈን እንመልከት።

(የቁጥር መረጃዎችን ያገኘሁት "አዙሪት" ከሚለው የሌፍተናንት ጀነራል ዮሐንስ ገብረመስቀል መፅሐፍ ነው)

የትግራዩ ጦርነት ባካለለባቸው አከባቢዎች 369,855 ቤቶች ላይ ጉዳት ደርሷል። ከእነዚህ ቤቶች ውስጥ 67 በመቶ የሚሆነው ሙሉ ለሙሉ ወድመው ከጥቅም ውጭ ህነዋል። ቤቶች ላይ የደረሰው ጉዳት ወደ ገንዘብ ሲቀየር 2.56 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር ይሆናል።

በጤና ተቋማት ላይ የደረሰው ጉዳትም ሰፊ ነው። ጉዳቱ ወደ ገንዘብ ቢቀየር 1.42 ቢሊዮን ዶላር ይሆናል።

ጦርነቱ ባከተተባቸው ቦታዎች በድምሩ 2681 ትምህርት ቤቶች ወድመዋል። መውደም ሲባል ሙሉ ለሙሉ መውም ነው። 4158 ትምህርት ቤቶች ደግሞ ቀላል እና ከባድ ጉዳት አስተናግደዋል። 4.2 ሚሊዮን ተማሪዎች ከትምህርት ገበታ ውጭ ሆነዋል። 200 ሺ መምህራን ከስራቸው ተፈናቅለዋል። የትምህሩ ዘርፍ የገጠመው ውድመት ወደ ገንዘብ ሲቀየር 1.74 ቢሊየን የአሜሪካ ዶላር ኪሳራ አስተናግዷል።

የሴፍቲኔት ፕሮግራም ላይም ጉዳት የደረሰ ሲሆን 114.88 ሚሊየን ዶላር ይደርሳል ጉዳቱ።
የባህልና ቱሪዝም ዘርፍ የገጠመው ጉዳት 454.1 ሚልዮን ዶላር ነው።
መብራት ብርቅ በሆነባት ሐገራችን ላዬ 48.67 ሚሊየን ዶላር ጉዳት በመብራት መሰረተ ልማት ላይ ደርሷል።
አይ ሲ ቲ ላይ የደረሰው ጉዳት 557.69 ሚለየን ዶላር ነው።

በጦርነቱ መንገዶች ፥ ድልድዮች ፥ የአውሮፕላን ማረፊያ ጉዳት ደርሶባቸዋል። ይህም ወደ ገንዘብ ሲቀየር 98.1 ሚሊየን ዶላር ነው።
የውሃ እና ፍሳሽ ላይ የደረሰው ውድመት 95 ሚሊየን ዶላር ነው። (ይህ ዘርፍ ከጤና ባለው ቀጥተኛ ግኑኝነት የተነሳ ሌሎች ጣጣዎችንም ማስከቱ አይቀርም)

ከመዘጋጃ ቤት አገልግሎት ጋር በተያያዘ 145. 8 ሚሊየን ዶላር ውድመት ደርሷል።

በሁለት እግሩ መቆም አቅቶት የሚኔገታገተው የእርሻ ዘርፍ 16.79 ቢሊዮን ዶላር ኪሳራ አስተናግዷል።
በንግድ ዘርፍ 274 ሚለየን ዶላር ውድመት እና 157 ሚለየን ዶላር ኪሳራ ደርሷል
ኢንዱስትሪ ዘርፍ 1.17 ቢሊዮን ዶላር ኪሳራ አስተናግዷል።

በፋይናንስ ዘርፍ 933 የባንክ ቅርንጫፎች ጉዳት አስተናግደዋል። ይህም 14 በመቶ የሚሆኑ የሐገሪቱ ባንኮች ተጎድተዋል። በገንዘብ 693.4 ሚለየን ዶላር ውድቀት ተፈጥሯል።

በ299 ወረዳዎች የሚገኙ መንግስታዊ ተቋማት ላይ 142.56 ሚለየን ዶላር ኪሳራ ደርሷል።

በተፈጥሮ ሀብት ላይ የደረሰው ጉዳት 715 ሚሊየን ዶላር ነው።

አደጋ ለመከላከል የሚውል የእህል ማከማቻ ፥ መድሃኒት ፥ ነዳጅ... ላይ የደረሰው ጉዳት 31.8 ሚሊየን ዶላር ነው።

ሐገራቼን ደሃ ናት። ኑሯችን ከእጅ ወደ አፍ ነው። በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንዲባል ከ27 ቢሊየን የአሜሪካ ዶላር በላይ የገንዘብ ኪሳራ ደሃዋ ሐገራችን አስተናግዳለች።

ሰብአዊ ኪሳራው ብዙ ነው።

የተደፈሩ ሴቶች ቁጥር መቶ ሺ ይሻገራል። መቶ ሺ ሴቶች እንደ ቀልድ ተደፍረዋል። የሞቱ ሰዎች ቁጥር ሚሊዮን ይሻገራል። አንድ ሚሊዮን ባለ ተስፋ እንደ ዋዛ ሞቷል። ጦርነቱ ባካለለው አከባቢ የተፈናቀለው ሰው ቁጥር ደግሞ 5.1 ሚለዮን ነው።

ከዚህ ሁሉ ምን ተማርን? መልሱ ምንም የሚል ይሆናል! ከአንዱ ጦርነት ሳናገግም ወደ ሌላ ጦርነት ገብተናል።

የትግራዩ ጦርነት የፈጠረው ብሔራዊ ቁስል ሳይሽር አማራ ክልል ውስጥ ጦርነት ተከፍቷል።

ከታሪክ የተማርነው ከታሪክ አለመማርን ነው!


@Tfanos
"እናቴ ትሙት"
(ተስፋኣብ ተሾመ)
* * *

ልጆች ነበርን። ሞትን በቅጡ እንረዳ ዘንድ እድሜያችን የማይፈቅድ ልጆች ነበር። የመሳፍንት እናት እንደሞተች የሰማነው ህይወት እና ሞት ድንበርተኞች መሆናቸውን በማናውቅበት ለጋነታችን ነው።

"የመሳፍንት እናት ሞተች" ተባለ እንደዋዛ።
"ሙዝ ገዝተን እንሂድ" አልን እንደ ቀልድ።
መሳፍንት ከቃለ- ህይወት ትምህርት ቤት ከዜሮ ክፍል ጀምሮ አብሮኝ የተማረ ጓደኛዬ ነው። ዜሮ ክፍል ቅደመ መደበኛ ትምህርት መሆኑ ነው። ዜሮ ክፍልን ስንሻገር አንደኛ ክፍልን እንሆናለን።
ቅዳሜ ቅዳሜ የቃለ ህይወት ሰንበት ተማሪዎች መፅሐፍ ቅዱስን በልጆች ቋንቋ እንማራለን። ከሰኞ እስከ አርብ ደግሞ ፊደል እንቆጥራለን።

ሶስተኛ ክፍል ሳለን የመሳፍንት እናት መሞቷን ሰማን። እንደ ቀላል ነገር "አስቱ ሞተች" አሉን። ታላላቆቻችን እትዬ አስቴር ይሏታል። እኛ ግን እንደ ቆሎ ጓደኛችን አስቱ እንላታለን።

አስር የመሳፍንት ጓደኞች "ትምህርት ቤት መዋጮ ተጠይቀናል" ብለን ፥ ከእናታችን መቀነት ሰርቀን ፥ ሀብታም ዘመዶቻችንን አስቸግረን ሁለት ብር ከሃምሳ ሳንቲም ሰበሰብን። እያንዳንዳችን ስሙኒ ስሙኒ ነበር ያዋጣነው።
በሰበሰብነው መዋጮ ሙዝ ገዝተን ለቅሶ ሄድን። ተሳቀብን። "የልጅ ነገር" አሉን አንዳንዶች።

"አስቱ" ስትሞት ያላለቀሰው ብቸኛ ሰው መሳፍንት ነው። ሁላችንም እንባ ስንራጭ ጥግ ላይ ሆኖ በመገረም ያየን ነበር። ወንድም እህቶቹ እየተነሱ ሲወድቁ እያያቸው ፈገግ ብሏል። ጎረቤት እንባ ሲራጭ ቲያትር እንደሚመለከት ታዳሚ በተመስጦ ተከታተላቸው።
ያ ሁሉ ሰው ሲያለቅስ መሳፍንት አላለቀሰም።
"እኛ እንኳ ስናለቅስ እርሱ ያላለቀሰው ምን አስቦ ነው?" ብለን ተናደንበታል። ለአስቱ ስላላዘነ አቂመንበት ነበር። ቂማችንን ፈጥነን ረሳነው እንጂ ልንጣለው ወስነን ነበር።

"ለእናቱ ያላለቀሰ ክፉ" አልነው መሳፍንትን።

አመታት አለፉ። አስቱ ከሞተች ስድስት አመት በኋላ መሳፍንት ወደ'ኛ ቤት መጣ።
"ተነስ ሳሚ" አለኝ።
"የት እንሂድ?"
"አስቱጋ ደርሰን እንመጣለን"
"የት?"
"መቃብር ቦታዋ"
እንደታዘዝኩት አደረግኩ።
አረም የበቀለበት ፥ ጥሻ የሆነ መቃብር ስፍራዋ ወሰደኝ። የአስቱ መቃብር ጋር ስንደርስ "እዚህ ቁም የምናወራው ነገር አለ" አለኝ።
"ከማንጋ ነው የምታወሩት?" አልኩት ግራ ገብቶኝ።
"ከአስቱጋ"
በግራ መጋባት ቆሜ ወደ መቃብሯ ተጠጋ። እናቱ መቃብር ጋር ቆሞ ያጉተመትም ጀመር።
እየፈራሁ ልጠጋው ስሞክር እንድመለስ በእጁ ምልክት ሰጠኝ። ግራ ቢገባኝ ራቅ ብዬ ቆምኩ። ለአንድ ሰአት ያህል ከመቃብሯ ጋር አወራ።

ወደ ቤታችን ስንመለስ "እንዴት ልትመጣ ቻልክ?" አልኩት።
"በየሳምንቱ እመጣለሁ" አለኝ በግድ የለሽነት
"ከመች ጀምሮ"
"ካረፈች ጀምሮ"
ዝም አልኩት። የምለው ሲጠፋኝ አቀረቀረቀርኩ።
"ሁሌ እመጣለሁ። ዛሬ ብቻዬን መምጣት ስላልፈለግኩ ነው ካንተጋ የመጣሁት" አለኝ
እንባዬን እንዳያየው ታገልኩ።

ይህ በሆነ በወሩ ቤታችን መጣ። ቤት ሲደርስ ከእናቴ ጋር ፀብ ገጥሜ አየኝ። ፊቱን አዙሮ ወጣ። ተከተልነው። እኔና እናቴ ተከተልነው።

"መሳፍንት አትሂድ" እናቴ አዘዘችው።
ቆመ። አቀርቅሮ እያለቀሰ ቆመ።
"ምን ሆነሃል?" እናቴ ነበረች ጠያቂዋ
"አንተ ቢያንስ የምትጣላት ፥ የምትናደድባት ፥ የምትጨቃጨቃት እናት አለችህ። እኔ ግን...." ሳግ ንግግሩን ገታው።
የማልቀሱ ተራ የሁለታችን ሆነ። እኔ እና እናቴ እኩል እንባ አፈሰስን።

የመሳሳፍንት ዘመዶች ለወንድም እና እህቶቹ ያዝናሉ። "የእናታቸው ሞት ጎድቷቸዋል" ይላሉ። ለመሳፍንት ግን የሚያዝን የለም። "እሱ በእናቱ ሞት አልተጎዳም። የሞተች ቀንም አላለቀሰም" ይሉታል። ዘመድ እና ጎረቤት ለሁለት ወንድሞቹ እና ለሁለት እህቶቹ ያዘነውን ሲሶ ያህል ለእርሱ አዝነው አያውቅም።

አመታት አለፉ። መሳፍንት ፍቅረኛ ያዘ።

አንድ ቀን ለፍቀረኛው "እናቴ ትሙት" ብሎ ማለላት። እየዋሻት መሰላት።
"በስርኣት ማልልኝ" አልችው
"እናቴ ትሙት" አላት በድጋሚ
"እናትህ ስንቴ ትሙት?" አለችው።
ይሄኔ ተስፈንጥሮ ተነሳ። እጆቹ ተንቀጠቀጡ፥ ጉንጮቹ ቀሉ፥ ሁለቱ አይኖች እንባውን አፈሰሱ።

እኛ እናውቀዋለን። መሳፍንትን እናውቀዋለን። "እናቴ ትሙት" ብሎ ከማለ እውነቱን እንደሆነ እናውቃለን። "እናቴ ትሙት" ብሎ እንደማይዋሽ እናውቃለን...


@Tfanos
@Tfanos
መቶ ሺህ ብር አሸነፍኩ።

ኢንጂነር ቤጃይ ኔርሽ ናይከር የመቶ ሺ ብር ስጦታ አበረከተልኝ። በብሩ የዩቲዩብ ፕሮግራም እንጀምርበት ነው የተሰጠኝ።

ቀጥሎስ? ጋዜጠኛ ወሰን ሰገድ ገብረኪዳን "እኔ ደግሞ ካሜራ ስጦታ እሰጥሃለሁ። ሲመችህ ና እና ውሰድ አለኝ"

ካሜራ እና መቶ ሺ ብር ስጦታ ተሰጠኝ ማለት ነው።

የተ ቻናሉ በቅርቡ ይጀመራል።
ወደ ገደ ለው

"ደርዘን ጥያቄዎች" የዪቲዩብ ዝግጅት በቅርቡ ስራ ይጀምራል። ደርዘን ጥያቄዎች አስራ ሁለት ርዕሰ ጉዳዮች ላይ የሚያተኩር ቁም ነገራም ፕሮግራም ነው። በእያንዳንዱ ክፍል እንግዳ ሆኖ ለሚቀርበው ተጋባዥ አስራ ሁለት ጥያቄዎች ይቀርባሉ።
ደርዘን ጥያቄዎች ለደርዘን ርዕሰ ጉዳዮች እንደማለት ነው።

ጥያቄዎች ደርዝ ያላቸው ፥ የተጋባዦችን እውቀት እና ልምድ ለመረዳት የሚረዱ እንዲሆኑ ጥረት ይደረጋል።

"ሰዎች መስማት የሚያገባቸውን ነገር መስማት በሚፈልጉበት መንገድ ማቅረብ" የፕሮግራሙ ዋና ነገር ነው።

ዩቲዩብ ቻናሉ ተከፍቷል። የመቶ ሺ ብር ሽልማቱ ዘር ነው። ያንን ዘር እናሳድግበታል።

ቻናሌን ሰብስክራይብ አድርጉ። ብትችሉ ለሌሎችም ብታስተዋውቁ እወዳለሁ።

በነገራችን ላይ፥ የመጀመሪያ እንግዳ ቢሆን የምትወዱትን መጠቆም ትችላላችሁ።


https://youtube.com/@tesfaab_teshome_offical?si=Xyt0J6tsqJM6LNN4
ዲፕሲክ የኢትዮጵያን ጉዳይ ሲጠየቅ አጥጋቢ መልስ እየሰጠ አይደለም። አንዳንዶች እየተቹት ነው።

ይልቁንስ ጣታችንን ወደራሳችን ነው ማዞር ያለብን።

ዲፕሲክም ሆነ መሰሎቹ ኢንተርኔት ላይ ያለ ብዙ መረጃ አኝከው እኛ ስንጠይቃቸው ከዚያ ውስጥ ያመነዥካሉ። ካዩት መረጃ አጠሬራ ነው የሚሰሩት። በሆነ ጉዳይ ደህና መልስ ከሌለ በቂ የሚማሩበት መረጃ (training data) የለም ነው።

ስለኢትዮጵያ ያንን ማዘጋጀት የራሳችን ጉዳይ ነው። ዊኪፔዲያን እንመልከት። የአውሮፓ የቀበሌ ሊቀመምበር ገጽ ከኛ ሃገር ሚንስትር ገጽ የበለጠ መረጃ አለው። ምን ያህላችን ዊኪፔዲያ ላይ እንጽፋለን?

ጠቅላይ ሚንስትር ሃይለማርያም ወደ ፌደራል መንግስት የመጡ ሰሞን (ምክትል ጠሚ ከመሆናቸው በፊት) ትምህርታቸውንና የደቡብ ክልል ፕሬዚዳንት እያሉ ከሆኑ ጉዳዮች የማውቀውን ያህል የዊኪፔዲያ ገጻቸውን ኤዲት አድርጌ ነበር። ያው ከአርባምንጭ ስለማውቃቸው ነሽጦኝ ነው ያኔ። ከዚያ መልስ ምንም አልጨመርኩበት ነበር። ጠቅላይ ሚንስትር እስኪሆኑ እነዚያ ሴክሽኖች ምንም ተጨማሪ ነገር አልተጻፈባቸውም ነበር።

ያኔስ የኢንተርኔት አጠቃቀም ሰፊ አልነበረም ይባላል። ዛሬ የዶክተር ስለሺ በቀለ ዊኪፔዲያ ገጽ 192 ቃላት ብቻ ነው ያሉት። አንድ ገጽ አይሞላም። እኔ እንኳ ልጻፍ ብል ቢያንስ አምስት ገጽ የማውቀው አይጠፋም። ከእኔ የበለጠ የሚያውቅ ሰው ብዙ አለ።

ከጥቂት አመታት በፊት ሃይስኩል ተማሪዎችን ስለየአካባቢያቸው እንዲጽፉ አርገው ጥሩ የሆኑት እየተመረጡ ዊኪፔዲያ ላይ ቢመጡ የሚል ሃሳብ መንግስት አካባቢ ላሉ ሰዎች ሰጥቼ ነበር። ወይ ሃሳቤ በወቅቱ ተልካሻ ነበር ወይ አይሰሙም። የትኛው እንደሆነ በሳይንስ አልተረጋገጠም።

የዶክተር ኤርጎጌ ተስፋዬ ዊኪፔዲያ ገጽ የዶክትሬት ዲግሪያቸውን ከህንድ እንዳገኙ ይገልጻል። ከየት ዩኒቨርስቲ እና በምን አመት የሚለው የለውም። በሳቸው እድሜ ላለ ሰው ይህ መረጃ የቅርብ ጊዜ መረጃ ነው። ያንን የሚያውቅ ጠፍቶ ነው ወይስ የሚገደው ጠፍቶ?

ሰሞኑን ኖራ ቀቡት ብለን አቧራ ስናስነሳ የነበርንበት ፋሲል ግቢ ሁለት ገጽ የማያልፍ መረጃ ነው ያለው። ጎንደር ውስጥ ደህና ካሜራ ያለው እንግሊዘኛ የሚጽፍ ሰው እጥረት የለም መቸስ። ዲሲን ያጨናነቀው የጎንደር ዲያስፖራስ ምን ይሰራል? ዘጠኝ ጊዜ ዳውን ዳውን ብሎ አስረኛው ላይ ቢጽፍ የዳበረ ገጽ ይኖረው ነበር ፋሲል።

ብዙ ምሳሌ መስጠት ይቻላል ግን እነዚህ በቂ ናቸው።

ይህ የእንግሊዘኛ ገጾቹን በተመለከተ ነው። በአማርኛ ከዚህችም ያነሰ ነው ያስቀመጥነው!

ለማንኛውም መአት መረጃ ተሰጥቶት መረጃውን አቀነባብሮ አጠሬራ የሚሰራ ቴክኖሎጂ ስለኛ ደህና መልስ ከሌለው ችግሩ ከቻይና ሳይሆን ከራሳችን ነው። ያላጎረስነውን እንዲተፋ እየጠየቅን ነው።

Via Temesgen Markos Kindo


@Tfanos
"በሚኒሊክ ስም የሚደረግ መሃላ ቅዱስ ነው"
(ተስፋኣብ ተሾመ)
* * *

የጣሊያን ወራ.ሪ በአድዋ አከርካሪው ከተመታ በኋላ ቂም ቋጠረ። መሸነፉ ጥርስ አስነከሰው። ለድፍን 40 አመታት የበቀል ዝግጅት ካደረገ በኋላ ኢትዮጵያን ለመው.ረር ተነሳ።

ፋሽ.ስቶች ሕግ ጥሰው ኢትዮጵያን ሲወሩ "ከኢትዮጵያ ጎን እንድንቆም ሐቅ እና ህሊና ያስገደደናል" ያሉ ጥቂት ፈረንጆች ነበሩ። ከነሱ መካከከል አንዱ አዶልፍ ፓርለሳክ ነው።

የቼክ ሪፐብሊኩ ተወላጅ አዶልፍ ፓርለሳክ ከኢትዮጵያ ጎን ተሰልፎ ለመዋጋት ወደ ሐገራችን መጣ። ከፋሽ.ስት ለመፋለም ነፍጥ አነሳ። በረሃ ወርዶ ተፋለመ።
ከአርበኞች ጋር በዱር በገደል ሲንከራተት ከርሞ በጦርነት እሳት ተለብልቦ በመጨረሻም "የሃበሻ ጀብዱ" የተሰኘ መፅሐፍ ያበረከተው ፈረንጁ አርበኛ ሐገራችንን ለመጠበቅ ከአባቶች እኩል ጀብድ ሰርቷል።

ከእለታት በአንዱ አዶልፍ ፓርለሳክ ከራስ ካሳ ጦር ተለይቶ ከጥቂት አጀቢዎች ጋር ሳለ በሽፍቶች ተከበበ። ከኢትዮጵያዊያን አጃቢዎቹ ጋር በመሆን እየተታኮሰ ለመሸሽ ሞከረ። ሽፍቶቹን አምለጠው ተራራ ላይ መሸጉ።
ተራራው ለዘላቂነት የሚኖሩበት አይደለም። ስንቅ የላቸውም። ከታች በሽፍታ ተከባዋል። ከሽፍቶቹ ራቅ ብሎ የወራ.ሪው ጣሊያን ጦር አለ።

የነ አዶልፍ ፓርለሳክ እጣ 3 ብቻ ነው።
አንድ፥ ተራራው ላይ ሆኖ በረሃብ መሞት። ሁለት፥ ተራራው ላይ እንዳሉ በአውሬ ተበልቶ መሞት።
ሦስት በትጥቅም በቁጥርም የሚበልጣቸውን ሽፍታ መፋለም።
የከበቧቸው ሽፍቶች በቁጥር ብቻ ሳይሆን በታጠቁት መሳሪያ ጥራት ይበልጧቸዋል። ከሽፍቶቹ ጥቂት ርቀው የጣሊያን ጦር ሰፈር አለ።

ፓርለሳክ ወደ ኢትዮጵያ ከመምጣቱ በፊት ጓደኞቹ አንድ ነገር ነግረውታል። "ወደ ኢትዮጵያ አትሂድ፥ እዛ ችግር ቢገጥምህ ሐበሾቹ አሳልፈው ይሰጡሃል" ብለውት ነበር። እሱ ግን አሻፈረኝ ብሎ ከኢትዮጵያውያን ጎን ሆኖ ሊፋለም ወደ ሐገራችን መጣ። አሁን እሱ እና ጥቂት ጓደኞቹ በጠላት ከበባ ወድቀዋል።

ለመፋለም ወሰኑ። ተፋልመን እናምልጥ ወይንም የጀግና አሟሟት እንሙት አሉ። በስፍራው የነበሩቱ "ፈረንጅ ጌታ ፥ አንተ እየመራኸን እንፋለማቸው" አሉት ተስማማ።

ቀጥለው በየተራ መሓላ ፈፀሙለት።

"በሚኒሊክ ስም እምላለሁ፥ እስከመጨረሻው እንፋለማለን። እኔን ሳይገድሉ ለሐገሬ ልትዋጋ የመጣኸውን አንተን አይገሉህም" እያሉ ማሉለት።
እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ "በሚኒሊክ ስም ቃል እንገባለን። በጀግንነት እንዋጋለን። ሁላችንም ሳንሞት አንተ አትሞትም" አሉት። አመናቸው።

አዶልፍ ፓርለሳክ በመፅሐፉ "በኢትዮጵያ ምድር በሚኒልክ ስም የሚገባ መሓላ ቅዱስ ቃል ነው። ሐበሻ በሚኒሊክ ስም ምሎ የገባውን ቃል በፍፁም አያጥፈውም" በማለት አስፍሯል።

መሓላውን ከፈፀሙ በኋላ በ3 ቡድን ተከፍለው ከከበቧቸው ጋር ተፈለሙ።

ፓርለሳክ ሲጓዝ ከፊት ሁለት ከግራና ቀኝ አንድ አንድ እንዲሁም ከኋላው አንድ ሰው ሆነው ይጓዛሉ። በመሬት ሲሳብ ይሳባሉ። ሲሮጥ ይሮጣሉ። ሲንበረከክ ተመሳሳዩን ያደርጓሉ።
እንዲህ የሚያደርጉት ከየትኛውም አቅጣጫ ጥይት ቢተኮስ ቀድመው ለመሞት ነበር።

በሶት ቡድን የተከፈሉ 20 የሚሆኑቱ ጀግኖች ከበባውን ሰብረው ሲያመልጡ ሁለት ሰው መስዋትነት ከፈለ። ሁለት አርበኞች የጀግና አሟሟት ሞቱ።

"በሚኒሊክ ስም እስከመጨረሻው ጠብታ እዋጋለሁ" ብለው የገቡትን መሓላ ፈፀመው ከከበባ አመለጡ።

ፓርለሳክ ምንድነው ያለው?

"ኢትዮጵያዊ በሚኒሊክ ስም የገባው ቃል ቅዱስ ነው። ምንግዜም አይሽረውም"

ድጋሚ የተለጠፈ

@Tfanos
ቢዝነሳችሁ በዳግም ልማት
ወይም ጦ^ርነት የተቃወሰባችሁ:-
=====================
1) ካሳ የምታገኙ ከሆነ ሞክሩ:: ግን እኛ ሀገር የሰነድ አደረጃጀታችን ለካሳ ስለማይመች ጊዜና ገንዘብ ባትፈጁ ይመከራል:: የሚያሰጥም ከሆነ እንደ አንድ ጉዳይ ያዙት እንጂ ሕይወታችሁ እዚያ ላይ አይንጠልጠል:: ባይሆን ጉዳያችሁን ተደራጅታችሁ ለጠበቃ ስጡት::

2) ፋይናንሻል ሪከቨሪ ላይ አተኩሩ

- ማቋቋሚያ ድርጅቶች, NGO, የወረዳዎች የሥራ ፈጠራ ተቋማትን ቅረቡ:: Soft loan ፈልጉ::

- ከአበዳሪዎቻችሁ ጋር ተደራደሩ:: የቀድሞ ብድር ሠርታችሁ እንድትከፍሉዋቸው እንዲያግዙዋችሁ አድርጉ እንጂ አትራቁ:: ስልክ ዘግቶ መጥፋት ለተጨማሪ ድብርት ይዳርጋል:: ስል ጭንቅላት ይዶለዱማል::

- ቀድሞ ሥራውን ስለምታውቁት በአጋር የሚያሠራችሁ ድርጅት ፈላልጉ:: የሦስት ዓመት ውል ግቡ::

- ከባንክ የተበደራችሁም ከባንኮቹ ጋር የብድር ሪስኬጁል እና አማራጮችን ተነጋገሩ:: የባንኮችን የሐራጅ ማስፈራሪያ አትፍሩት:: አንድ ባንክ maximum ሐራጅ የብድሩ 5% ብቻ ነው:: በአብዛኛው NPL (Non performing loan) 3% አካባቢ ነው:: ለራሳቸው ሲሉ ይተባበሩዋችሗል::

3) ድጋሚ ሥራችሁን ጀምሩ

- ተመሳሳይ መረበሽ የማይገጥመው ሰፈር ወይም ከተማ በመቀየር ያንኑ ሥራ ጀምሩት:: ከመጀመራችሁ በፊት ቢያንስ ሦስት ቦታ ሂዱ:: የመሬት ማኔጅመንት, ፕላን ኮሚሽንና የኮሪደር ልማት ጽሕፈት ቤት ጠይቁ

- የወትሮ ሥራ ለምትሄዱበት ሰፈር የማይገጥም ከሆነ ሪብራንድ አድርጉት:: ስሙን ቀይሩት ለማለት ነው:: ለሰፈሩ የሚመች ሐሳብ ለማፍለቅ መንደሩን በመኪና ዙሩት::

- ከስተመር ቤዝ ቀይሩ:- ወትሮ በጨረታ ወይም walking customers እየሸጣችሁ ነበር ይሆናል:: አሁን ጨረታውም online ሆኗል:: የሶሻል ሚዲያ የሽያጭ አማራጮች ጥሩ ናቸው::

- የጎንዮሽ የተለያየ ቢዝነስ አማትሩ

- ባልና ሚስት ብቻ ሳይሆ ልጆችም ከሶሻል ሚዲያ scrolling ጋብ ብለው ይሥሩ:: በቴክኖሎጂ ያግዙዋችሁ::

- ዕድሜያችሁ ገና ከሆነ ለተወሰነ ጊዜ ከሀገር ወጣ ብላችሁ ምጡ::

4) ሳይኮሎጂያዊ ዝግጅት

- በቅርብ ዓመታት ውስጥ ሕይወቱን ያጣ በሚሊዮን የሚቆጠር ዜጋ አለን:: እናንተ ግን በሕይወት አላችሁ:: ብዙ የምትነግሩት ታሪክ አላችሁ:: ብትጽፉት, ብትገጥሙት, ብትዘፍኑት, ብትስሉት የሚደንቅ ዘመን አልፏል:: ተስፋ አትቁረጡ:: አመስግኑ::

- በዚህ ወቅት አጠገባችሁ የነበረ ጓደኛችሁን እንዳትጥሉት:: ተያያዙ:: መከራ በዘነበ ማግስት ያለ ጥርጥር ጸደይ ይመጣል:: ይህ የዓለም ተፈጥሯዊ አካሄድ ነው::

- በተቻለ መጠን ከሱስ ተላቀቁ:: At least ቀንሱ:: ጮማ ሲቆርጥ የነበረ ሆድ እንጀራ በጨው እምቢ አይልም:: ሱስ ግን በተቸገሩ ወቅት ይብስ ያስቸግራል:: ይህ ምናልባትም ከሱስ መላቀቂያ ምቹ ወቅት ሊሆን ይችላል::

- የኃይማኖት መሪዎች ቢበላሹ እንኳ መጻሕፍቱ አሉ:: ትጉና ጸልዩ:: ዱዓ አድርጉ::

ስላዳመጣችሁኝ አመሰግናለሁ::

Via Abdulkadir Hajj Nureddin


@Tfanos
2003 አ.ም የዘጠነኛ ክፍል ተማሪ ነበርኩ። (እንደ ቀልድ አረጀሁ😥)

ያኔ በብዙ መከራ የቆጠብኩትን ሃምሳ ብር ይዤ መፅሐፍ ቤት ሄድኩ፥ ኦሮማይን ልገዛ።

"ኦሮማይ መፅሐፍ አለ?" አልኩ
"አለ፥ ዋጋው ስልሳ ብር ነው"
ደነገጥኩ። ስልሳ ብር ሙሉ ከየት አመጣለሁ?
በቀስታ ተመለስኩ። እያዘገምኩ ተራመድኩ።
"ወንድም ና" አለኝ መፅሐፍ ቤቱ ውስጥ መፅሐፍ ሲመርጥ የነበረ ሰው። ተመለስኩ።
"ለምን ተመለስክ?"
"ሃምሳ ብር ብቻ ነው ያለኝ"
"በሀምሳ ብር ይሸጥልሃል"
"ከሆነ እሺ"
ሻጩ መፅሐፉን ሰጠኝ። ሃምሳ ብሩን ልከፈል ሳወጣ "እኔ እከፍልልሃለሁ" አለኝ ሰውዬው። ሳላመነታ "ፍቅር እስከ መቃብር ስንት ብር ነው?" አልኩ። "ስልሳ ብር ነው ግን ሃምሳ ብር እሸጥልሃለሁ" አለኝ መፅሐፍ ነጋዴው። ይሄኔ ኦሮማይን የገዛልኝ ሰውዬ "ፍቅር እስከመቃብርንም እኔ እገዛልሃለሁ" አለኝ። አመስግኜ ሁለቱን መፅሐፍ ወሰድኩ። እንደ ቀልድ መቶ ብርን የሚያህል ነገር ኢንቨስት አደረገ።

ሃምሳ ብሯን ላለማባከን በማግስቱ አሸባሪው የሚል መፅሐፍ እና ሌላ ርዕሱን የረሳሁት መፅሐፍ ገዛሁ።

ዛሬ ሁለት መፅሐፍ ለመግዛት 2 ሺ ብር ስከፍል ያ አጋጣሚ ትዝ አለኝ። መፅሐፍ ስልሳ ብር ሙሉ መግባቱ ተአምር ሆኖብኝ ለሰው ሁሉ ያወራሁትን አስታወስኩ። "እንዴት ስልሳ ብር መፅሐፍ ይሸጣል?" ብዬ ነበር። ማንበብ የሃብታሞች ብቻ እየሆነ መስሎኝ ነበር።

(በእርግጥ ይሄ ከእናንተ ህይወት ጋር ምንም አይገናኝም ይሆናል


@Tfanos
ጥንት በሐገራችን የነገስታት ቤተሰቦች ተመርጠው የሚታሰሩበት ተራራ ነበር። ምክኒያቱ ልዩ ነው። በዚህ ጉዳይ የአልቫሬፅን መፅሐፍ አጣቅሼ የዩቲዩብ ፕሮግራም ሰርቻለሁ። አድምጡት።

በነገራችን ላይ ደርዘን ጥያቄዎች ወደ እናንተ መቅረብ ሊጀምር አብዛኛው ዝግጅት ተገባዷል። ደርዘን ጥያቄዎች ከመጀመሩ በፊት ግን ሶስት የማሟሟቂያ ዝግጅቶች በዩቲዩብ ቻናሌ ይለቀቃሉ። የዛሬው የመጀመሪያ ማሟሟቂያ ነው። ገብታችሁ አይታችሁት ላይክ እና ሼር ብታደርጉ ደግሞም በዩቲዩብ ገፄ ስር አስታያየት ብታሰፍሩ ይረዳኛል።


https://youtu.be/jslnyNp8iYw
አንዳርጋቸው ፅጌ "ነፃነትን የማያውቁ ነፃ አውጪዎች" የሚል መፅሐፍ አለው። ርዕሱን እወደዋለሁ። (በእርግጥ መፅሐፉም ብዙ ሊያወያይ የሚገባ መፅሐፍ ነው)

"ነፃነትን የማያውቁ ነፃ አውጪዎች" የሚለው ርዕስ ፖለቲካችንን ገላጭ ነው። ፖለቲካችን ሰፈር ያሉ ሰዎች ጭቆናንን በማውገዝ የሚታውቁ ዳሩ ግን ጨቋኝ ናቸው። ስለ ዴሞክራሲ ይለፈልፋሉ ፥ ነገር ግን ፀረ ዴሞክራሲ ናቸው።

በየዘመኑ በሐገራችን የተደረጉ ለውጦች የሚፈለገውን ለውጥ እንዳያመጣ ካደረጉ ምክኒያቶች መካከል አንዱ "ለውጥ አራማጅ" ተብዬዎቹ ፀረ ዴሞክራሲ መሆናቸው ይመስለኛል።

ንጉሡን ገርስሰው ስልጣን ላይ የወጡት በዝባዥ ፥ ህዝብ አስለቃሽ ፥ ዜጋ ገ ዳ ይ ወዘተ ነበሩ። ደርጎች "ኢትዮጵያ ትቅደም" ብለው እየፎከሩ ኢትዮጵያዊያንን አሰቃይተዋል።

ደርግን ተቃውመው ስልጣን ያገኙት በብሔር ብሔረሰቦች ስም እየማሉ ብሔሮችን ሲረግጡ ነበር። ለዴሞክራሲ እንደታገሉ እየለፈፉ የመብት ጥያቄ ያነሱት ላይ ቃታ ለመሳብ አልፈሩም።

ህወሃትን ከሰይ..ጣን አስተካክለው ፕሮፕጋንዳ ሲነዙ የነበሩቱ በመንበር ላይ በተገኙ ማግስት ኢ-ሰብአዊ ለመሆን ሁለቴ አላሰቡም።

ዛሬ ብልፅግናን ከሚቃወሙት መካከል ቀላል ቁጥር የሌላቸው ጨቋኝ እና ጨካኝ ናቸው። "የኔ ደጋፊ ያልሆነ የኔ ባለጋራ ነው" ብለው እንደሚያስቡ ነገረ ስራቸው ይመሰክራል። ትችትን መቀበል አይችሉም። በሃሳብ ከሚለያቸው ጋር ለመወያየት ፈቃደኝነቱ የላቸውም።

"የሚያጠግብ እንጀራ ከምጣዱ ያስታውቃል" አይደል የሚባለው? ነገ ስልጣን ላይ ሲወጣ አንባገነን የሚሆን አካል ዛሬ በተቃውሞ ወቅት ማንነቱ ይታወቃል።

Nb አሳዬ ደርቤ የብዙ ተቃዋሚዎች ማሳያ ነው!
ነገ ልደቴ ነው። ከሁላችሁም ቀላል የልደት ስጦታ እፈልጋለሁ።

ደርዘን ጥያቄዎች በቅርቡ ይጀምራል። (በቅርቡ ማለት አበዛህ ማለት አይቻልም😀)
ለደርዘን ጥያቄዎች የቀረፃ ቦታ ማዘገጃጀትን ጨምሮ የቅደመ ዝግጅት ስራዎች ተሰርተው ተጠናቀዋል። በቀጣይ ሳምንት ቀረፃ እንጀምራለን። (ነገ የሙከራ ቀረፃ ከሰራን በኋላ ሙሉ ቀረፃ በሳምንቱ መጨረሻ ይጀመራል) ቀጥሎ ወደ እናንተ ይቀርባል።

(በእርግጥ ደርዘን ጥያቄዎች ወደ ቴሌቪዥን ፕሮግራም የሚያድግበት በጣም ጠባብ እድልም አለ 😎)

ለማንኛውም ልደቴን ምክኒያት በማድረግ የዩቲዩብ ቻናሌን ሰብስክራይብ ብታደርጉ እና ብታስደርጉ ደስ ይለኛል።

(ብሶት የወለደው የህዝብ ልጅ ተስፋኣብ ተሾመ ለሰፊው ህዝብ ጥቅም ሲባል የካቲት 3 ተወልዷል

የዩቲዩብ ቻናል

https://youtube.com/@tesfaab_teshome_offical?si=Xyt0J6tsqJM6LNN4
ሰዎች የሚቀልዱት ቀልድ የንቃተ ሂላናቸውን ደረጃ ያሳያል።

በተለይ የመብት ጥሰት ሲፈፀም በጉዳዩ ላይ ቀልድ ለመፍጠር የሚሞክሩ ሰዎች ያልሰለጡ ፥ ለሌላ ሰው ደንታ የማይሰጣቸው ፥ ሃላፊነት የማይሰማቸው ወዘተ ናቸው።


@Tfanos
"አባት ላደረገው መልካም ነገር የማይመሰገን፥ ባላደረገው ነገር የሚወቀስ ነው"

ከላይ ያለውን አባባል ያነበብኩበትን መፅሐፍ ዘንግቼዋለሁ። (አዲሱ እድሜዬ በፈጠረብኝ እርጅና የተነሳ እየረሳሁ ነው😀)
አባባሉ ይገርማል። ስለ አባቶች ብዙ ይነግረናል።

ሰሞኑን ዝም ብዬ ስለ አባትነት አስባለሁ። ስለ አባቶች አወጣለሁ ፥ አወርዳለሁ። ሳር ቅጠሉ "አባትነት ምን ማለት ይሆን?" ብዬ እንደጠይቅ ይገፋኛል። (በእርግጥ እኔ ለልጆቼ ምን አይነት አባት እሆን ይሆን ብዬ አስቤያለሁ 😎😀)
ተጨባጭ መልስ የለኝም።

ፕሮፌሰር ጌታቸው ሀይሌ በህይወት ታሪካቸው መፅሐፍ ላይ ያሰፈሩት ግሩም ገጠመኝ አለች። ከአእምሮዬ መቼም የማትጠፋ ታሪክ ነች።

ጌታቸው ሀይሌ ልጅ ሳለ ትምህርት እንዲማር ዘመድ ዘንድ ተላከ። የሄደበት ቦታ አልተስማማውም። ጌታቸው እንደ ሎ*ሌ ሆነ። አስከፊ ችግር ገጠመው። ሰውነቱ እስኪቆስል ድረስ ማከክ የየለት ተግባሩ ሆነ።

ከወቅቶች በኋላ ጌታቸው ሀይሌ ወደ አባቱ ሄደ። አባቱ መቃብር ቤት ነው የሚኖረው። ጌታቸውም ከአባቱ ጋር መቃብር ቤት ይኖር ጀመረ።
ከምሽቶች መካከል በአንዱ ለመተኛት ጌታቸው ልብሱን ሲያወልቅ በማከክ ብዛት የጌታቸው ሰውነት ላይ የተፈጠረውን ቁስል አባት ተመለከቱ። ይሄኔ አባት ፊቱን አዙሮ በመኝታ ልብስ ተሸፍኖ አለቀሰ።

"እንዳላየው ተከልሎ አለቀሰ" ብለዋል ፕሮፌሰር ጌታቸው ሀይሌ።

ስለ ልጁ መጎዳት የሚያለቅስ ፥ ግን ደግሞ እንባውን ልጁ እንዳያይበት የሚከለል አባት...

ይህች ታሪክ ከአእምሮዬ አትጠፋም። ከፕሮፌሰር ጌታቸው ሀይሌ የህይወት ታሪክ መፅሐፍ ላይ ቀድሜ ማስታውሳት ይህችን ታሪክ ነው። ስለ አባትነት የምትናገረው ብዙ ነገር አላት።

ብቻ ሰሞኑን ስለ አባትነት ደጋግሜ ሳስብ ነበር።

ያሰብኩትን በትክክል ከመፃፌ በፊት ሃሳቤ ተበታተነ መሰለኝ። የተበተነውን ሃሳብ ቅርፅ ሰጥታችሁ አንብቡት በቃ 😎


@Tfanos
"ክፉ ቀኖች ያልፋሉ ፥ ፅኑ ሰዎች ያልፉታል"
(ተስፋኣብ ተሾመ)
* * *

ሀ፥ በህወሓት እና በኦነግ መካከል ያለው የፖለቲካ ሽኩቻ የመስዋዕት በግ ፈለገ። ሁለቱ እንዲሸናነፉ ያለ ሀጢያቱ የሚታረድ ሚስክን ተፈለጎ ተገኘ። ያ ምስክን በሀረርጌ ገጠራማ አከባቢ የተከበረ አባት ነው።ሰውዬው እንደዋዛ "ኦነግ ገደ*ለው" ተብሎ ተገ*ድሎ ተጣለ። የሰውዬው ሞት ቤተሰባዊ ምስቅልቅል ወለደ።

ጥላዬ ታደሰ የተባለ ሰቃይ ተማሪ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተማሪ ነበር። የአባቱን ሞት የሰማ ቀን ሰማይ ተደፋበት። ተስፋው ጨለመ፥ የመኖር ፍላጎቱ ትቶት ተሰደደ።
ጥላዬ ታደሰ ከአባቱ ሞት በኋላ ሌላ ሰው ሆነ። ሙሉ ለሙሉ ሱስ ውስጥ ተዘፈቀ። ጫት ፥ ሲጃራ እና አረቄ መደበቂያው ሆኑ። ሀዘኑን በአረቄ ሸሸገው።

ጥላዬ ሱሰኛ ሆነ ሲባል ዝም ብሎ ሱሰኛ አይደለም የሆነው። አንድ እሁድ እለት እስኪሰክር ጠጥቶ ተኛ። ከስካር ወለድ እንቅልፉ የነቃው ሰኞ ሳይሆን ማክሰኞ ነው። ከእሁድ እስከ ማክሰኞ በእንቅልፍ አሳለፈ። ሰኞ እለት ሳይኖርባት አለፈች። ጥላዬ ታደሰ ሲሰክር እዚህ ድረስ ነው።

የአባት ሞት ፥ ተስፋ መቁረጥ ፥ ሱሰኝነት ፥ ብተኝነት እየተፈራረቁ የደቁሱት ዶክተር ጥላዬ "ጥላዬ ቀደምኩት" የሚል ህይወቱን የሚናገር ግሩም መፅሐፍ አለው። "ይህ ሰው ማነው?" የሚል ጠያቂ ካለ ዶክተር ጥላዬ ዛሬ የተከበረ የናሳ ሳይንቲስት ነው። አዎን የናሳ ሳይቲስት!

ህይወቱ ከሱስ እስከ ናሳ በአስገራሚ ክስተቶች የተሞላ ነው። የዶክተር ጥላዬ ህይወት የሚነግረን ግሩም መልእክት አለ! ያም መልእክት "ክፉ ቀኖች ያልፋሉ፥ ፅኑ ሰዎች ያልፉታል" የሚል ነው።

ለ፥ ፓስተር ታምራት ሀይሌ "አባት" ብለን ብንጠራቸው ከማያሳፍሩን ጥቂት የሃይማኖት ሰዎች መካከል አንዱ ነው። በወንጌላውያን አማኞች ዘንድ እጅግ የከበረ ስም ካላቸው ግንባር ቀደም ሰዎች መካከል አንዱ ፓስተር ታምራት ሀይሌ ነው።

የፓስተር ታምራት የትላንት ህይወቱ በብዙ ፈተና እና ውጣ ውረድ የታጨቀ ነበር።
አባቱ ታዋቂ ባለ ውቃቢ ነበር። ያ ብቻ ሳይሆን የአባቱ ውቃቢ እንዲያርፍበት ታምራት ተመረጠ። ከዚህ በኋላ ህይወቱ የሰቀቀን ሆነ። ገና በልጅነቱ ከእኩዮቹ ጋር በነፃነት መንቀሳቀስ የማይችል ሆነ። መናፍስት እየተገለፁለት ያሰቃዩት ነበር።

ቤተሰቦቹ ለሊት ለሊት ወንዝ ዳር እየወሰዱት የአምልኮ ስርኣት ፈፅመውበታል። ሰውነቱን እስኪቆስል በአሸዋ ከፈተጉት በኋላ በውሃ ይነከራል። የልጅ ሰውነቱ ላይ የተፈጠረው ቁስል ውሃ ሲያገኘው ስቃይ ቢፈጥርበትም ለውቃቢው ሲባል ደጋግሞ አድርጎታል።

ታምራት ወደ አዲስ አበባ ከመጣ በኋላ በሰው ቤት ተቆጥሮ ሲሰራ ከሰው በታች ሆኖ ተዋርዷል፥ ስድብ እና ዱላን እንደዋዛ ተቀብሏል። ራሱን ስለማጥፋት አስቦም ያውቃል።

ዛሬ ላይ ፓስተር ታምራት የተከበረ ሰው ነው። "የታምራት አምላክ ተአምረኛ" የሚል የህይወት ታሪኩን የሚያወሳ መፅሐፍ አለው።
የታምራት ህይወት ምን ይነግረናል? "ክፉ ቀኖች ያልፋሉ!"

ሐ፥ ኢትዮጵያ ከምትኮራባቸው ጥቂት የላቁ አእምሮዎች መካከል አንዱ ፕሮፌሰር ጌታቸው ሀይሌ ነው። ፕሮፌሰር ጌታቸው በቀላሉ የማይደገሙ ሊቅ ናቸው። ብቻቸውን ብዙ ሰው!

ጌታቸው ገና ጨቅላ ሳለ የፋሽስት ወረራ ቤተሰባዊ ምስቅልቅልን ወለደ። ከዛ በኋላ ብዙ አስቸጋሪ ወቅቶችን አሳልፏል።

አባቱ ለትምህርት ካላቸው ፍቅር የተነሳ ልጃቸው እንዲማር ዘመድ ዘንድ ሰደዱት። ውጤቱ ግን የተገላቢጦሾ ሆነ። ህፃኑ ጌታቸው መማር አልቻለም። እረኝነት እጣ ፈንታው ሆነ። በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንዲሉ የመማር መብቱን የተነፈገው ህፃን ሰብአዊ ክብሩንም ተቀማ። ሰውነቱ በእከክ ሲወረር አዛኝ አጣ። ሰውነቱ እስኪቆስል ድረስ ማከክ ግዴታው ሆነ።

ወደ አባቱ ሲመለስ የተከበረ ኑሮ አልጠበቀውም። ከአባቱ ጋር በመቃብር ቤት እየኖረ መማር እጣ ፋንታው ሆነ።

ጌታቸው ሀይሌ የእናቱን ፍቅር ሳይጠግብ ገና ጨቅላ ሳለ እናቱ ተለይታው ሄደለች። የእናት ናፍቆቱን የሚወጣበት በቂ እድል አልነበረውም።
አባቱ የጤና እክል ገጥሞት ከአልጋ መዋል ግዴታው ሲሆን ብቻውን ለአባቱ ቂጣ እየጋገረ ይኖር ነበር። እንደ እኩዮቹ መጫወት ሳያምረው አባቱን እያስታመመ እና ለአባቱ ምግብ እያበሰለ ልጅነቱን አሳልፏል።

ትዳር ከመሰረተ በኋላ ሐገር ለማገልገል በሚጥርበት ዘመን የደርግ ሰዎች ሊይዙት ቤቱ ድረስ ከመጡ በኋላ ተታኩሰው ጉዳት አድርሰውበታል። ፕሮፌሱሩ ለረጅም ዘመን በዊልቸር እንዲቀመጥ ያስገደደውን መዘዝ ያመጣው ያ ጉዳት ነበር።

ከዚህ ሁሉ በኋላ ግን ፕሮፌሰር ጌታቸው ሀይሌ ባለ ግርማ ሊቅ ሆነዋል። የስኬት ጫፍ ላይ ተገኝተዋል። ህይወታቸውን "አንዳፍታ ላውጋችሁ" በሚል መፅሐፍ ከትበውታል።

ህይወታቸው ምን ይነግረናል? ክፉ ቀኖች ያልፋሉ!

ሁላችንም በአንዳች አይነት መከራ እያለፍን ይሆናል። እጅ የማይሰጥ ፅኑ መሆን እንዳለብን የብዙዎች ህይወት ይነግረናል!

በእርግጥ ክፉ ቀኖች ያልፋሉ!

Nb፥ ሁለተኛ ደረጃ ተማሪ ሳለው "ክፉ ቀኖች ያልፋሉ ፥ ፅኑ ሰዎች ያልፉታል" የሚል የትርጉም መፅሐፍ አንብቤ ነበር። የመፅሐፉ ደራሲ ሮበርት ሹርለ ይመስለኛል።

@Tfanos
@Tfanos
"ተፈራ ሻሎም ሞተ" ተባለ። እንደዋዛ ሞቱን ፌስቡክ ላይ አነበብን።

የሻሸመኔ ልጅ ሆኖ ተፈራን የማያውቅ ማን አለ? በተለይ የዘጠናዎቹ ልጆች ሁሉም ያውቁታል ቢባል ነገሩ ትንሽ ማገነን ያለበት እውነት ይሆናል።

ሻሸመኔ ላይ ሻሎም ጁስ ቤት ስመ ጥር ጁስ ቤት ነው። ዛሬ ላይ ሻሎም ጁስ አቄጣጫ መጠቆሚያ ፥ የሰፈር መጠሪያ ፥ የባጃጅ ፌርማታ ወዘተ ሆኗል። ጁስ ቤቱ የተፈራ ነበር።

በህይወቴ ለመጀመሪያ ጊዜ ጁስ የቀመስኩት ሻሎም ጁስ ቤት ነው። ከአንዱ ዘመዳችን ጋር ሻሸመኔ ሸዋበር ቃለ ህይወት ቤተክርስቲያን ሄደን። በዛን ወቅት ወደ ሻሸመኔ በእንግድነት የመጣ ጴንጤ ማክሰኞ እለት ሸዋበር ቃለህይወት ቤተክርስቲያን መሄድ ልማዱ ነው። የፓስተር ጌቱ ዱሬሳ አገልግሎት ተናፋቂ ስለሆነ ሁላችንም በጉጉት አገልግሎቱን እንካፈላለን።

ያኔ እድሜዬ 10 ወይም 11 እያለ ከዘመዳችን ጋር ቃለ ህይወት ሄደን ስንመለስ ወደ ስመ ጥሩ ሻሎም ጁስ ቤት ሄድን። አስተናጋጅ መጥታ ትዕዛዝ ተቀበለችን። ነገሩ ግር አለኝ። ዘመዴ ስፕሪስ ሲል ሰመቼ እኔም ሰፕሪስ አልኳት። ጁሱን ጠጣን። ተፈራ ወደ እኛ መጥቶ "ምን ጎደለ?" አለን። አስገምጋሚ ድምፁ ፥ ወንዳወንድነቱ ታተመብኝ። የመጀመሪያዬ ጁስ የሻሎም ስፕሪስ ሆነ።

ተፈራ "ኪያን አገባት" ተባለ። ኪያ የጎረቤታችን እትዬ አስቴር ልጅ ናት። እትዬ አስቴርን አዴ እንላታለን። የቀበሌያችን ሊቀመንበር ነበረች። ደርባባ ሴት ናት። እንወዳታለን። በሰፈራችን ቴሌቪዥን ካላቸው ጥቂት ሰዎች መካከል አዴ አንዷ ናት። ቤታቸው ሄደን ቴሌቪዥን እናያለን። ሻይ ትሰጠናለች።
የአዴ ልጅ ሙሉ ጌታ የሰፈር ልጆችን ሰብስቦ ኳስ እና ሩጫ ያወዳድረናል። ላሸናፊዎቹ ደስታ ከረሜላ ይሸልማል።
የአዴ ልጅ ኪያ ደግሞ ሱቅ ትልከናለች። ኪያ አንዳንዴ ቸርች አብራኝ ትሄዳለች። ተፈራ መልከቀናዋን ጎረቤታችንን ኪያን አገባ። ያኔ ሰፈራችን መምጣት ጀመረ።

ከእለታት በአንዱ ተፈራ ቤታችን መጣ። ከአባቴ ጋር የተለያዩ ጉዳዮችን ማውራት ጀመሩ። ተፈራ ሲያወራ ግርማ ሞገስ ስላለው በተመስጥኦ እሰማቸዋለሁ።

ተፈራ በወቅቱ ይወቀስበት የነበረ ጉዳይ ነበር። ምን ያህል ብር እንዳተረፈ በሀቅ ለገቢዎች ስለ ሚያሳውቅ ጂ ል ይሉት ነበር። ትልልቅ ሆቴሎች ገቢ ቀንሰው ሲናገሩ እሱ እውነቱን ይናገራል። በዚህ የተነሳ ግብሩ ይጨምርበታል። አባቴ ለምን እንደዚህ እንደሚያደርግ ጠየቀው።

"ጌታ አይወድም። መፅሐፍ ቅዱስ ግብር እንዳጭበረብር አይፈቅድም። እግዚአብሔር ያለኝን ከባረከልኝ ይበቃኛል" አለ። ገረመኝ።

ስምንተኛ ክፍል ሆነን ተፈራ ጋር ሄደን። መዝሙር እየሰማ ደረስን። ተዋወቅነው። "የምህረት ልጅ ነህ አይደል?" አለኝ። ደስ አለኝ። "ምህረት የፀሎት ሰው ናት ፥ ጌታ ይባርካት" አለ። በደንብ ደስ አለኝ።

ጉዳያችንን ነገርነው። "ሰሊሆም የሚባል የስነ ፅሁፍ ህብረት አለን። መንፈሳዊ ፕሮግራም እናዘጋጃለን። ለፕሮግራማችን ትንሽ ገንዘብ እርዳን" አልነው።
ወደ ቢሮ ወሰደን። እጁን ጭኖ ፀለየልን። "እግዚአብሔር ወጣትነታችሁን ይጠብቀው፥ ዘመናችሁ ይለምልም" አለን። ቃል በቃል እንዲህ ነው ያለን። በሞገሳም ድምፁ ባረከን። ጁስ ጋበዘን። ከጠየቅነው በላይ ሰጠን።

"ለወደፊቱ ነጋዴ ከሆናችሁ ግብር እንዳታጭበረብሩ ፥ ለሐገራችሁም ለእግዚአብሔርም ታመኑ" አለን። ደስ አለን።

አንድ የማውቀው ሰው "ቸገረኝ" አለው። "ጊዚያዊ ነገር ከምሰጥህ እኔ ጋር ስራ ጀምር" አለው።
አንዳንድ ሰዎች ብር ሲጠይቁት በነፃ ከመስጠት ይልቅ ስራ ያሰራቸው ነበር።

የሆነ ጊዜ ተፈራ መክሰሩ ተነገረ። ብዙ ገመናዎች አደባባይ ላይ ዋሉበት። አሳዘነኝ። አንድ ቀን ፀጉሩ ድሬድ ሆኖ ፥ ፂሙ ጎፍሮ አየሁትና ደየገጥኩ። አቅፎ ሰላም ሱለኝ ሆድ ባሰኝ።

ከወራት በፊት ሻሸመኔ ስሄድ ካፌ ውስጥ አገኘሁት። በአክብሮት ሰላም ካለኝ በኋላ "እንደ ድሮው አሁንም ትፅፋለህ?" ብሎ ጠየቀኝ። ደስ አለኝ።

አንድ ቀን ልጁን መንገድ ላይ አገኘኋት። በደንብ ሰላም ተባባልን። "ምህረት እና ዳዊት ደህና ናቸው?" አለችኝ። "ኪያ ደህና ናት ወይ?" አልኳት። ከተለየኋት በኋላ "የተፈራን ስልክ ስጭኝ ባልኳት ምን አለ?" አልኩ።

የሆነ ቀን ደውዬለት ባወራው ብዬ አስብ ነበር። ዛሬ ጠዋት የኪያ ወንድም ሙሉ ጌታ ደወለልኝ። ስልኩን እንደ ዘጋሁት አጠገቤ ላለችው ስለ ቤተሰባቸው ነገርኳት። "ሰሞኑን ለተፈራ እደውላለሁ" ብዬ አሰብኩ።

ፌስቡክ ስገባ መሞቱን አየሁ። ተፈራ ሞቷል ተባለ እንደ ዋዛ

@Tfanos
ባለፈው ሀረር ነበርኩ።

እንደ ማንኛውም የሀረር ተጓዥ ከጅቦችጋ ፎቶ ተነሳሁ

ጅብ ያስፈራል? ኧረ አያስፈራም! አይደለም ጅብ ሰውም አልፈራ።

እኔ በሐገሬ አይደለም ጅብ ሰውም አለምዳለሁ 😎

ልፅፍ ያሰብኩት ነገር ነበር። ከጀመርኩ በኋላ ተምታታብኝ

እረዲያ
ነገረ አባት
(ተስፋኣብ ተሾመ)
* * *

"እግዚአብሔር አባታችሁ ነው የሚለውን ትምህርት በደንብ የተረዳሁት ልጅ ከወለድሁ በኋላ ነው"

ከላይ ያለውን የተናገረው የመፅሐፍ ቅዱስ አፈታትን ያስተማረን ፓስተር ነበር። መጀመሪያ ስሰማው ነገሩን እንደ ጥሩ ግነት ቆጥሬ አለፍኩት። ከወራት በኋላ ሌላ መምህር 'ክርስቲያናዊ ጋብቻን' ሲያስተምረን 'ልጅ ስወልድ የእግዚአብሔር አባትነትን አጣጣምኩት' አለን። ያኔ ነገሩን ከልቤ ልመዘግብ ተገደድኩ። ሁለት የተወደዱ መመህራን ተመሳሳይ ሃሳባቸው ከልቤ ታተመ።

አመታት አለፉ። ነገሩ በልቤ እንደተፃፈ፥ በአእምሮዬ እንደተመዘገበ አራት አመታት እንደ ወዛ ሄዱ።

የህይወት ታሪክ መፅሐፍት ማንበብ እወዳለሁ። እድሜያቸው የገፉ ፥ በህይወት ውጣ ውረድ ያለፉ፥ ስኬትን የተጎናፀፉ ሰዎችን ታሪክ ማንበብ ያስደስተኛል። ከንባብ ዘርፍ ዋነኛ ምርጫዬ ህይወት ታሪክ ማንበብ ነው። (እንዲህ ከሆነማ የህይወት ታሪክ መፅሐፍት ስጦታ እሰጥሃለሁ የሚል ሰው ይበረታታል😎)

የህይወት ታሪኮችን ሳነብ በብዙዎቹ ዘንድ ተመሳስሎሽ አገኛለሁ። ስኬታማ ሰዎች ሁሉ ሊባል በሚያስችል ደረጃ ፦ ደፋር እና ተጋፋጭ ፥ ሃላፊነት የሚወስዱ ፥ በአስቸጋሪ ሁኔታ ተስፋ የማይቆርጡ ፥ እውቀትን የሚራቡ ፥ አርቀው የሚያልሙ ሆነው አገኛለሁ። 'ህይወት ታሪክን ከማንበብ ምን ተማርክ?' የሚል ጠያቂ ቢመጣ ከላይ የጠቀስኳቸውን እሴቶች ተማርኩ እላለሁ።

ሌላ ነገር፥

የብዙ ሰዎች ህይወት ላይ የአባትን በጎ ተፅዕኖ አገኛለሁ። ሲዲኒ ሸልደን ራሱን እንዳያ*ጠፋ ያደረገው የአባቱ ንግግር ነበር። ፕሮፌሰር ጌታቸው ሀይሌ እውቀትን የሚራቡ ሰው የሆኑት በአባታቸው ተፅዕኖ ነው። ከታላላቅ ኢትዮጵያዊያን መካከል የሆኑት ደጃዝማች ወልደ ሰማዕት ከአባታቸው ስርኣትን ተምረዋል። አፄ ሀይሌ ስላሴ በህይወት ታሪካቸው መፅሐፍ እንደነገሩን ከሆነ ከአባታቸው የተማሩት ብዙ ነው።

በብዙ ስኬታማ ሰዎች ጀርባ የአባት አሸራ አለ። (ወይም ያለ ይመስለኛል)

የህይወት ታሪክ መፅሐፍትን ሳነብ የልጆች እጣ ፈንታ ላይ አባቶች ያላቸውን አይተኬ ተፅዕኖ ለማመን ተገድጃለሁ። በብዙዎች መፅሐፎች ላይ ያለውን የአባት ባህሪ ጨምቄ ለመገመገም ብሞክር ሁሉም በጎ አባቶች የሚጋሩት ጥቂት ነጥብ አለ።

ቀጪ ናቸው። ልጆች ከመስመር ሲወጡ ለመቅጣት አያመነቱም። የቤተሰብን ሸክም የሚሸከሙ ናቸው። በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ እንኳን ቤተሰባቸውን ይሸከማሉ።
የልጆቻቸውን ነገ ቀድመው ለመስራት ይጥራሉ። መሪነት አይለያቸውም። ወዘተ...

ብዙ በጎ አባቶች ባህሪያቸው የሚያሰለች መስሎ ሊታይ ይችላል። ግን ደግሞ የልጆቻቸውን እጣ ፈንታ ይሰሩታል።

የገባኝ ነገር "ምናልባት ውጤታማ አባቶች ከፍቅር በላይ ክብር የሚገባቸው ናቸው" ብዬ ማሰብ ጀምሬያለሁ።
ተናገረው የሚደመጡ ፥ አጥፊን የሚቀጡ ፥ ሲቆጡ የሚፈሩ ፥ ድንበርን ማስመር የሚችሉ ፥ በትንሽ በትልቁ የማይበረግጉ ወዘተ...ናቸው።

እንግዲህ እኔ አባት አይደለሁም። ስለ አባትነት ማውራት አያምርብኝም ይሆናል።

ሰሞኑን የደጃዝማች ወልደ ሰማዕት ገብረወልድን ህይወት ታሪክ ሳነብ ነበር። ዛሬ ካፌ ተጎልቼ 'ህይወት ታሪኮችን ማንበብ ምን ጠቀመኝ?' ብዬ ራሴን ጠየቅኩ። ከህይወት ታሪክ መፅሐፎች ውስጥ ያገኘሁትን የጋራ እሴቶች ለማስታወስ ሞከርኩ። ከጋራ እሴቶች መካከል አንዱ አባትነት ሆኖ አገኘሁ።

እንደ እኔ ባለ ባላገባ ፥ ባልወለደ ሰው አንደበት ስለ አባትነት ማብራሪያ መስጠት አግባብ እንዳልሆነ አውቃለሁ...


@Tfanos
"ሰሞኑን ስለ አባትነት ደጋግመህ ፃፍክ። የተጀመረ ነገር አለ ወይ?"

አንዳንድ ሰዎች በልባቸሁ ካሰቡባችሁት የተቀነጨበ 😎😀
2025/02/25 15:59:05
Back to Top
HTML Embed Code: