tgoop.com/wubTarikoch/18
Last Update:
ነባት
ክፍል1
(መዚዳ ተማም)
በእውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሰረተ
ነባት እንደሁል ጊዜዋ የፈጅር ስግደት ጥሪ (አዛን) ከመውጣቱ ተነስታለች. የስግደት ትጥበት (ውዱ) አድርጋ የፈጅር ስግደት አካሄደች.
እንደጨረሰች እጆቿን ከታፋዋ ላይ ሳታነሳ እንባዋ ከትላልቅ አይኖቿ ስር ሁለት ሁለት መስመር እየሰሩ መውረድ ጀመሩ. ሁኔታዋን ላየ ሰው የ18ዓመት ለጋ ወጣት ሳትሆን የችግር ዶፍ ያስተናገደች እናት ነው ምትመስለው.
ከጌታዋ ጋር የነበራትን ንግግር ስትጨርስ ከመስገጃዋ አጠገብ ባለው ፍራሽ ላይ የተኛውን ታናሽ ወንድሟን በፍቅር እያየች በትዝታ 3ዓመት ወደ ኋላ ተጓዘች እናትዋ፣አባትዋ፣እሷ እና ታናሽ ወንድሟ ሳሊም አንድ ላይ ሆነው በጠባብዋ ቤታቸው ውስጥ በሰፊ ፍቅር አሳልፈውት የነበረው ቆንጆ ጊዜ ትዝ ብልዋት ፈገግ አለች .
ከአንዱ የትዝታዋ ጓዳ ወታ ማስታወስ ወደማትፈልገው ግን ግድ ወደሚሆንባት የትዝታዋ ክፍል ገባች .
እንባዎቿ በቅፅበት ከአይኖቿ ወረዱ .
ያቀን እናትዋን ለመጨረሻ ጊዜ የተሰናበተችበት ቀን ነበር. የዛን ቀን ማታ የኢሻ ሶላት እንደሰገዱ ነበር እናትዋ ለነሱ የተሻለ ሂወት እንደሚገባቸውና ወደ አረብ ሀገር በመሄድ ይህን እንደምታሳካ አስረድታ ለሊት 8ሰዓት እንደምትበር የነገረቻት ነባት ድንጋጤዋን በለቅሶዋ ነገረቻት እናት የልጅዋን ለቅሶ ባትችልም ለሷ ስትል መሄድ ነበረባት የአንድ አመት ለጋ ህፃን የሆነውን ሳሊምን ጥላባት ሄደች ከመሄድዋ በፊት ለአባትዋ ያለችው ንግግር ሁሌ ታስታውሰዋለች
"ውዴ በናትንና ሳሊምን አደራ" የአባትዋ ፀባይ መለወጥ ሆድ ይብሳትና እንባዎቿ ፍጥነት ጨምረው ይወርዳሉ እንባዋን በእጇ ጠረገችና አይኗን ከሳሊም ፊት ሳታነሳ ጎንበስ ብላ ሳመችው .
የፀሀይዋ ጨረር በበሩ ስንጥቅ አድርጎ መንጋቱን አረዳት ሲከፈት ሚንጫጫው በር ጩዕትና እሱን ተከትሎ እሚመጣው ያባትዋ ግልምጫ ሰልችቷታል ግን ደግሞ አባትዋ ሲነቃ ቁርስ አቶ ከሚመታት ግልምጫውን ትመርጣለች
ወደ ውጭ ለመውጣት በሩን ከፈተች በሩም የለመደውን እሪታውን ለቀቀው አባትዋም የተለመደውን ግልምጫውን ወረወረ "አንቺ ሳትፈለጊ የተወለድሽ አንቺ እያለሽ እዚ ቤት መተኛት አይቻልም?"
ከአፉ በጣም የሚያስጠሉ ቃላቶች ይወጣሉ አሁን አሁን በናት ስለለመደችው ነው እንጂ የሱን የቃላት ውርወራ ተከትሎ እንባዋ ያንኳኳ ነበር መቼም ማይለመድ ነገር የለም ለምዳዋለች.
እንደተለመደው ከቤታቸው ጎን ለማብሰያነት የተሰራው ዳስ ላይ ቁርስ አበሰለች ሳሊምን አጥባ ቁርስ አበላችው
አባትዋ 4ሰዓት ላይ እየተነጫነጨ ከእንቅልፉ ነቃ የበናት እናት እያለች የፈጅርን ሶላት ሰዓቱን ጠብቆ ባይሰግድም በውትወታዋ ፀሀይ ከወጣች በውሀላ ይሰግዳል
ተነስቶ ፊትና እጁን ታጥቦ "አንቺ ልጅ ቁርስ አታመጪም?"
"ባባ አስገብቼልሀለው እኮ"
በቃ ሂወታቸው በዚህ እሽክርክሪት ውስጥ ከሆነ እነሆ 3ዓመቱ
የነባት አባት አብረውት ቅጠል ሚያኝኩ 3ጓደኞች አሉት ቀን ውለውበት ማታ 7ሰዓት ሊደርሱ ይችላሉ ታድያ በዚህ ሰዓት ጋባዣ አሱ ነው.
እናትዋ በሰው ሀገር የሰው ፊት እየገረፋት የምትሰበስባቸውን ሳንቲሞች አባትዋ አፈር ድሜ ያበላዋል.
እሱም ሳያንሰው ከጓደኞቹ ሲያረፍድ ነባትን እንድትካድም እንቅልፍ ከልክሎ ከጓደኞቹ ጋር ሚያወሩትን በሷ እድሜ መስማት ያልነበረባትን አስቀያሚ ንግግራቸውን ለመስማት ትገደዳለች
እናትዋን ሲያጥላላ፤ስለ ልጃ ገረዶች ውበት ሲያወራ ነባት ልቧ ለሁለት ይከፈላል የአባትዋን ክፋት፤የእናትዋን የዋህነት ታስብና ተደብቃ ታነባለች
ቢያንስ የናፈቀቻትን እናትዋን በስልክ ሊያገናኛት ፍቃደኛ ቢሆን በቂዋ ነበር እሱ ግን ከዚህ ይልቅ የሆነ ያልሆነ ምክንያት ደርድሮ በመሀከላቸው ክፍተት መፍጠሩን ተያይዞታል
ምሽቱ ለንጋት ቦታውን ለቀቀ
የነባት አባት ቁርሱን በልቶ ከቤት ሲወጣ ነባት ልብስ እያጠበች ነበር
"እሱን ትተሽው ቤቱን አስተካኪው በኋላ ሚመጣ ሰው አለ"
"እሺ አባ" ብላው ወደ ቤት ገባች ቤቱን አፅድታ ለእንግዳ ሚሆን ምግብ አብስላ ጠበቀችው
አባትዋ ከአንዲት ወጣት ሴት ጋር መጣ እንደሌላ ጊዜው ተኮፍሶ አልነበረም የመጣው .
እየፈገገ "ነባት ነይ ተዋወቅያት ዘመድሽ ነች"
"እሺ ነባት እባላለው ግን የማንነች?"
ተኮሳትሮ "ዘመድ ነች አልኩሽ አይደል"
ነባት ውስጧ ደስ ሳይለው ተዋወቀቻትና እቤት ገቡ
ነባት ምሳ አቅርባላቸው እንደ ሁልጊዜው ለሷ እና ለሳሊም ለብቻ አቀረበች ምሳ ከበሉ በኋላ ነባት ሳሊምን ይዛ ወጣች የነባት አባ ከልጅቷ ጋር መሳሳቅ ጀመሩ ነባት እና ሳሊም በር ላይ የቤቱን ግድግዳ ተደግፈው ቁጭ ብለዋል ነባት የሳሊምን ራስ እየደባበሰች እየረበሻት ያለውን ሳቃቸውን መንስዔ ትፈለፍላለች
"ባባ እኮ እንዲ ሲስቅ ካየውት 3ዓመት አለፈ ግን ለኛ እንዲ ለምን አይስቅልንም ቆይ ምን አድርገንበት ነው?" ራሷ ጠይቃ ራሷ ስትመልስ "ወይስ በኔና ሳሊም እየሳቁብን ነው?" ሳቃቸው እንባዋን ገፋው መስመር እየሰራ ከጉንጯ ወረደ
ነባት ሳታስበው ሳሊምን ጥላው በሀሳብ ሄዳ ስለነበር ሳሊም መተኛቱን አላስተዋለችም ከሀሳብዋ ስትመለስ ሳሊም ራሱን ታፋዋ ላይ ጥሎ ተኝቷል እንባዎቿን በመዳፎቿ ጠረገቻቸውና ሳሊምን አቅፋ አንስታ ወደ ቤት ለመግባት አንድ እግሯን ስታስገባ ወጣቷ ልጅ በአባትዋ .....
ይ ቀ ጥ ላ ል
ሌሎች ልብ-ወለዶችን ለማንበብ👇
https://www.tgoop.com/joinchat-qpK2kr8UdrRlNjI0
BY ውብ ታሪኮች®
Share with your friend now:
tgoop.com/wubTarikoch/18