tgoop.com/Wahidcom/3952
Last Update:
የአክብሮት ስግደት
በአሏህ ስም እጅግ በጣም ሩኅሩህ እጅግ በጣም አዛኝ በሆነው።
41፥37 ሌሊት እና ቀን ፀሐይ እና ጨረቃ ከምልክቶቹ ናቸው፥ ለፀሐይ እና ለጨረቃ አትስገዱ! ለእዚያም ለፈጠራቸው ለአሏህ ስገዱ፡፡ እርሱን ብቻ የምታመልኩ እንደ ኾናችሁ ለሌላ አትስገዱ፡፡ وَمِنْ آيَاتِهِ اللَّيْلُ وَالنَّهَارُ وَالشَّمْسُ وَالْقَمَرُ ۚ لَا تَسْجُدُوا لِلشَّمْسِ وَلَا لِلْقَمَرِ وَاسْجُدُوا لِلَّهِ الَّذِي خَلَقَهُنَّ إِن كُنتُمْ إِيَّاهُ تَعْبُدُونَ
"ሻኻህ" שָׁחָה የሚለው የዕብራይስጥ ቃል፣ "ፕሩስኩኔኦ" προσκυνέω የሚለው የግሪክ እና "ሡጁድ" سُّجُود የሚለው የዐረቢኛ ቃል "ስግደት"prostration" ማለት ነው፥ ለአንድ አምላክ በሁሉም ስፍራ የሚቀርበው ስግደት የአምልኮ ስግደት ሲሆን ለፍጡራን በአካል ሲገናኙ ለሰላምታ የሚቀርበው ስግደት የአክብሮት ስግደት ነው፦
ዘፍጥረት 23፥7 አብርሃም ተነሣ፥ "ለ-"ምድሩ ሕዝብ እና "ለ-"ኬጢ ልጆች "ሰገደ"። וַיָּ֧קָם אַבְרָהָ֛ם וַיִּשְׁתַּ֥חוּ לְעַם־הָאָ֖רֶץ לִבְנֵי־חֵֽת׃
እዚህ አንቀጽ ላይ አብርሃም ለ-"ምድሩ ሕዝብ እና ለ-"ኬጢ ልጆች ያቀረበውን የአክብሮት ስግደት "ሻኻህ" שָׁחָה ሲሆን በግሪክ ሰፕቱአጀንት "ፕሩስኩኔኦ" προσκυνέω በዐረቢኛ "ሡጁድ" سُّجُود ነው። ስለዚህ "አሏህ ለመላእክት ለአደም ስገዱ" ሲል "የአክብሮት ስግደት ነው" ስንል እርር እና ምርር ብላችሁ የሚያንጨረጭራችሁ እና የሚያንተከትካችሁ ምን ይውጣችሁ ይሆን? እንቀጥል፦
ዘፍጥረት 27፥29 አሕዛብ ይገዙልህ ሕዝብም "ይስገዱልህ"። יַֽעַבְד֣וּךָ עַמִּ֗ים [וְיִשְׁתַּחוּ כ] (וְיִֽשְׁתַּחֲו֤וּ ק) לְךָ֙ לְאֻמִּ֔ים
እዚህ አንቀጽ ላይ ይስሐቅ ያዕቆብን “ይስገዱልህ” ሲለው "ያምልኩህ" ማለቱ ነው? የዮሴፍም ወንድሞች ለዮሴፍ በምድር ላይ በግምባራቸው ተደፍተው ሰገዱለት፦
ዘፍጥረት 42፥6 የዮሴፍም ወንድሞች በመጡ ጊዜ በምድር ላይ በግምባራቸው ተደፍተው "ሰገዱለት"። וַיָּבֹ֙אוּ֙ אֲחֵ֣י יֹוסֵ֔ף וַיִּשְׁתַּֽחֲווּ־לֹ֥ו אַפַּ֖יִם אָֽרְצָה׃
ለዮሴፍ እንደተሰገደለት ተጨማሪ ጥቅስ ዘፍጥረት 43፥26 ዘፍጥረት 43፥28 ዘፍጥረት 44፥14 ተመልከቱ! ሩት ለቦኤዝ በግምባርዋም ተደፍታ በምድር ላይ ሰገደችለት፦
ሩት 2፥10 በግምባርዋም ተደፍታ በምድር ላይ ሰገደችለት። וַתִּפֹּל֙ עַל־פָּנֶ֔יהָ וַתִּשְׁתַּ֖חוּ אָ֑רְצָה
ከዚህ ሁሉ የሚገርመው ከአንዱ አምላክ ከያህዌህ ጋር ለእሴይ ልጅ ለንጉሡ ለዳዊት ራሳቸውን አዘንብለው ሰገዱ፦
1ኛ ዜና 29፥20 ራሳቸውንም አዘንብለው ለያህዌህ እና ለንጉሡ ሰገዱ። וַיִּקְּד֧וּ וַיִּֽשְׁתַּחֲו֛וּ לַיהוָ֖ה וְלַמֶּֽלֶךְ׃
"ሰገዱ" በሚል በአንድ ግሥ እና "እና" በሚል መስተጻምር ተጫፍሮ መጥቷል፥ ስግደቱ ለያህዌህ የአምልኮት ለዳዊት ደግሞ የአክብሮት ነው። በእስራኤል ባህል ለሰላምታ እርስ በእርስ በግምባር ተደፍቶ መስገድ የተለመደ ነው፥ 1ኛ ሳሙኤል 20፥41 1ኛ ሳሙኤል 25፥23 2ኛ ሳሙኤል 18፥28 2ኛ ሳሙኤል 19፥18 1ኛ ነገሥት 1፥23 ተመልከት!
በአዲስ ኪዳን የአክብሮት ስግደት ቀጥሏልን? እንዴታ ያለ ጥርጥር ቀልሏል፥ ሐዋርያት ለኢየሱስ የአክብሮት ስግደት ሰግደውለታል፦
ሉቃስ 24፥52 እነርሱም፤ ሰገዱለትና በብዙ ደስታ ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሱ። καὶ αὐτοὶ προσκυνήσαντες αὐτὸν ὑπέστρεψαν εἰς Ἰερουσαλὴμ μετὰ χαρᾶς μεγάλης,
እዚህ አንቀጽ ላይ "ስግደት" ለሚለው የገባው ቃል "ፕሩስኩኔኦ" προσκυνέω ሲሆን ኢየሱስ በሰጠው ምሳሌ ውስጥ ዕዳውን መክፍል ያልቻለው ባሪያ ለጌታው መስገዱ በእስራኤል ባህል ስግደት አክብሮትን ለማመልከት እንደሚመጣ ጉልኅ ማሳያ ነው፦
ማቴዎስ 18፥26 ስለዚህ ባሪያው ወድቆ "ሰገደለትና"፦ ጌታ ሆይ፥ ታገሠኝ፥ ሁሉንም እከፍልሃለሁ" አለው። πεσὼν οὖν ὁ δοῦλος προσεκύνει αὐτῷ λέγων Μακροθύμησον ἐπ’ ἐμοί, καὶ πάντα ἀποδώσω σοι.
BY ወሒድ የዕቅበተ ኢሥላም መጣጥፍት"Wahid Articles of Islamic Apologetics"
Share with your friend now:
tgoop.com/Wahidcom/3952